Wednesday 17 July 2013

የአዉሮጳ ኅብረት ምክር ቤት ልዑካን የኢትዮጵያን እስር ቤቶች እንዳይጎበኙ ተከለከሉ።

የአዉሮጳ ኅብረት ምክር ቤት ልዑካን የኢትዮጵያን እስር ቤቶች እንዳይጎበኙ ተከለከሉ። አሶሲየትድ ፕረስ ከአዲስ አበባ እንደዘገበዉ ልዑካኑ ቀደም ሲል እስር ላይ የሚገኙ ጋዜጠኞችንና የፖለቲከ ኞችን ለመጎብኘት ፈቃድ አግኝተዉ ነበር። በጀርመናዊቱ የምክር ቤቱ እንደራሴ በባርብራ ሎህቢለር የተመራዉ የኅብረቱ የሰብዓዊ መብቶች ኮሚቴ ልዑካን ቡድን በሶስት ቀን ቆይታዉ  ከኢትዮጵያና ከአፍሪቃ ኅብረት ባለስጣናት ጋ ተነጋግሯል። ከኢትዮጵያ የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር፣ የምክር ቤት አፈ ጉባኤ፤ እና የኢትዮጵያ የሰብዓቂ መብቶች ኮሚሽን እንዲሁም የመብት ተሟጋቾች ጋ የአገሪቱን የሰብዓዊ መብት ይዞታ አስመልክቶ ተወያይቷል። ዶቼ ቬለ ያነጋገራቸዉ የቡድኑ መሪ ባርብራ ሎህቢለር ኢትዮጵያ ዉስጥ መሻሻሎች መኖራቸዉ እንደማይካድ በመጠቆም ይጎድላል ያሉትን እንዲህ ገልጸዋል፤
«በመጀመሪያ መሠረታዊ የሰብዓዊ መብትን ለምሳሌ የመማር መብትና የመሳሰሉትን ማረጋገጣቸዉን አድንቀናል፤ ሆኖም በመልዕክታችን የጸረ ሽብር ህጉን የጸጥታ ስጋት ያልሆኑና ትችት የሚሰነዝሩ ወገኖችን ወደወህኒ ለማዉረድ አትጠቀሙበት፤ በተጨማሪም ትርጉም ያለዉ ስራ እንዳይሰሩ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን የሚያግደዉን ህግ እንዲያሻሽሉ ወይም እንዲያነሱ፤ ከዚህ ሌላ በሰላማዊ መንገድ ስለተቃወሙ ወይም መንግስትን በአንድም በሌላ መልኩ ስለተቃወሙ ብቻ የታሰሩትን እንዲፈቱ ጠይቀናል።»
ልዑካኑ እስረኞችን እንዲጎበኙ ከተፈቀደላቸዉ በኋላ የተከለከሉበት ምክንያት በዉል አልተገለፀም። ቀደም ሲል ከአፍሪቃ ኅብረት የፖለቲካ ኮሚሽነርና የጸጥታ ጉዳይ ባለስልጣናት ጋ በመገናኘትም በአካባቢዉ የሰብዓዊ መብቶች አያያዝ ላይ እንዲሁም የሁለቱ አህጉር ኅብረቶች ትብብርን አስመልክተዉ መወያየታቸዉ ተገልጿል።

Sunday 14 July 2013

እኔ ማነኝ?

እኔ ማነኝ? 
ማሳሰቢያ 

ይህን አነስተኛ ሰነድ የተወሰደው ከ220 ገጾች በላይ ርዝማኔ ካለው የግንቦት 7 ህዝባዊ ሃይል የፖለቲካ ስልጠና ሰነድ ነው። ዋናው የስልጠናው ሰነድ እኔ፣ እኛና ህዝባዊ ሰራዊቱ፣ ሃገራችን ኢትዮጵያ፣ የፖለቲካና የፍልስፍና ጽንጸ ሃሳቦችና ንድፈ-ሃሳቦች በሚሉ 4 ምእራፎች የተከፋፈለ  ነው።  በዚህ ተቀንጭቦ በቀረበው ሰነድ ውስጥ የተነሱ ጉዳዮች አንዳቸውም ሳይቀሩ የግንቦት ሰባት ህዝባዊ ሃይል ድርጅትና አባላት ብቻ ጉዳዮች ናቸው ብለን አናምን። የሁሉም የሃገራችን የፖለቲካ ድርጅቶችና አባሎቻቸው፣ እንዲሁም የአጠቃላይ የማህበረሰባችን ጉዳዮች ናቸው ብለን እናምናለን። በዚህ ሰነድ ውስጥ በተነሱ ጉዳዮች ላይ የግንቦት 7  ህዝባዊ ሃይል አባላት የሚያደርጉትን ሰፊና ጥልቅ ውይይት በትንሹም ቢሆን በማህበረሰባችን ውስጥ እንዲደረግ ካስቻልን ለሁላችንም ጠቀሜታ የሚኖረው መስሎናል። በዚህ አጋጣሚ ለማሳሰብ የምንፈልገው በዚህ ሰነድ ውስጥ የተነሱ ችግሮች በመሰረቱ ሊቃለሉ የሚችሉት ተገቢ የሆኑ የስርአት ለውጦችና ተገቢው የሆኑ ተቋማት ሲመሰረቱ እንደሆነ እናውቃለን።  ቁልፍ  የሆኑት ከፖለቲካው ጋር የተያያዙ የስርአትና የተቋማት ለውጦች ናቸው። ከዚህ አንጻር ነገሮችን ካየናቸው ይህን አይነቱ ሰነድ ወይም ሌላ ምንም አይነት ሰበካ፣ ትንታኔ፣ ውይይት፣ የንባብና የምርምር ጥረት መሰረታዊ የሆነውን ለውጥ ለብቻቸው ያመጣሉ ብለን አናምንም።  ችግሩ  ያለው  የምንመኛቸውን  መሰረታዊ  ለውጥ  ሊያመጡ  የሚችሉ  ስርአቶችና  ተቋማት  በሃገራችን  የሉም።  እነሱን  ደግሞ  የምንፈጥራቸው እኛው የሃገሪቱ ዜጎች ነን። ይህ ሰነድ ሌላው ሁሉ ቢቀር በግለሰብ፣ በቡድንና በድርጅት ደረጃ ችግሮቻችን ምን ያህል ጥልቅና ውስብስብ  እንደሆኑ  መገንዘብ  እንድንችል  ያደርገናል  የሚል  እምነት  አለን።  ችግሮቹን  ከተገነዘብን  የመፍትሄዎቻቸውን  ፍንጭ  ለማየት አያዳግተንም። ስለሆነም ይህን ሰነድ ከግንቦት 7 ህዝባዊ ሃይል ውጭ የሚገኙ ወገኖቻችን እንዲያነቡት በማሰብ በስፋት እንዲሰራጭ ወስነናል:: አንብባችሁ ሌሎች እንዲያነቡትና ውይይት እንዲያደርጉበት የተቻላችሁን ጥረት እንድታደርጉ በአክብሮት እንጠይቃችኋለን።  

የፖለቲካ  ስልጠና 

ምእራፍ 1- እኔ 

የፖለቲካ ሥልጠና ትምህርታችን የሚጀምረው እኔ በሚለው ርዕስ ነው። ለምን ይህ ርዕስ ከሁሉም ርዕሶች ቀደመ? በዚህ ርዕስ ሥር ምን  ጉዳዮች እናነሳለን? በመጨረሻም የዚህን ርዕስ ወይይት ስንጨርስ ምን መጨበጥ ወይም ማግኘት ይቻላል ብለን እናምናለን? የሚቀጥለው  ሃተታ ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ የሚሰጥ ይሆናል። 

1.  ለምን እኔ በሚለው ርዕስ  ጀመርን? 

መልሱ ቀላል ነው። ሁላችንም ወደ ግንቦት 7 ሕዝባዊ ኃይል ስንመጣ በግላችን ነው የመጣነው። ከሌሎች ጓደኞቻችን ጋር ብንመጣም ሕዝባዊ   ኃይሉን እንቀላቀል የሚለውን ውሳኔ  የወሰንነው እያንዳንዳችን በተናጠል ነው። ብዙዎቻችን ከዚህ በፊት አንተዋወቅም። የመጣነው እያንዳንዳችን ከሌላው ጋር ሆነን፣ ድርጅት ፈጥረን፣ ወያኔን ተዋግተን እናስወግዳለን ብለን አስበን ነው። ከተሰባሰብን በኋላ ከተናጠል ወደ ብዙሃን ተቀይረናል። ከእኔ እኛ ሆነናል። የእኛነታችን መሠረት ግን እኔ ነው። የእኛነታችን መነሻ እኔ ሆኖ መድረሻችን ደግሞ እኛ ሆኗል። መነሻውን የማያውቅ መድረሻውን አያውቅም ይባላል። እኔን ሳናውቅ እኛን ማወቅና እኛን መሆን አይቻልም። በመሆኑም እኔ ማነኝ የሚለውን ጥያቄ በቅድሚያ በሚገባ ለራሴ መመለስ መቻል ይኖርብኛል።  ከሌሎቹ ጓዶቼ የሚቀርብልኝ አንተ ማነህ የሚል ጥያቄ  በሚገባ መመለስ የምችለው ስለራሴ ከሚኖረኝ ጥልቅ እውቀት በመነሳት ብቻ  ነው። እውን ስንቶቻችን ነን እራሳችን በደንብ የምናውቅ? እኔ ማነኝ ለሚለው ጥያቄ  የተሟላ መልስ ለመስጠት ትልቅ ድፍረትና ከራስ ጋር መፋጠጥን ይጠይቃል። ጀግንነትን ይጠይቃል።  ከራስ ስሜት፣ ዝንባሌና ፍላጎት ጋር መሟገት ያስፈልጋል። የራስን አእምሮና ነፍስ መበርበር ያስፈልጋል።  

እኔ ማነኝ ለሚለው ጥያቄ በሚገባ መልስ ስሰጥ ነው ነገ በጦር ሜዳ ጓዴን ጥዬ እንደማልሸሽ፣ ወንድሜን በሰላሳ ሽልንግ እንደማልሸጥ እርግጠኛ የምሆነው። ወያኔ እንዳደረገው ነፃ አወጣዋለሁ የምለውን ሕዝብ መልሼ ረጋጭ መሆን እንደማልችል የማውቀው። ዘራፊ፣ ገፋፊ፣ አስገድዶ ደፋሪ እንደማልሆን እርግጠኛ መሆን የምችለው። ሰለ ሀገሬ ስለወገኔ መዋረድ የማነበንባቸውን ቃላት፣ ጉልበቱ እድሉ ስልጣኑ ሲኖረኝ ወደ በጎ ተግባራት እንደምቀይራቸው እርግጠኛ የምሆነው ራሴን በሚገባ ሳውቅ ነው። ጽናት ኖሮኝ የምዘልቅ፣ ምንም ፈተናና ችግር ወያኔን ከመደምሰስ ሊያስቆመኝ እንደማይችል እርግጠኛ የምሆነው እራሴን በሚገባ ሳውቅ ብቻ ነው:: ለጓዴ፣ ለድርጅቴ ለሃገሬ ሰዎችና ለሃገሬ የገባሁትን ቃል የማላጥፍ እንደሆነ  እርግጠኛ  የምሆነው እኔ ማነኝ ለሚለው ጥያቄ አጥጋቢ መልስ ስሰጥ ነው።  

እኔ ማነኝ የሚለውን ጥያቄ በሚገባ ለራሴ ስመልስ ከጓዶቼ የሚቀርብልኝን አንተ ማነህ የሚል ጥያቄ በቀላሉና በእርግጠኛነት መመለስ እችላለሁ። እኔ፣ የእኛ የግንቦት 7 ሕዝባዊ አባላት ስብስብና ድርጅት፣ ከዛም አልፎ የማኅበረሰባችንና የሀገራችን የመሠረት ድንጋይ ነው። የመሠረት  ድንጋይ ብቻ አይደለም። ድርጅታችንን፣ ማኅበረሰባችንና ሀገራችንን የምንገነባበት እያንዳንዱ ጡብ እኔ ነው። እኔ በደንብ ካልተገነባ፣ እኔ በደንብ  ካልታነጸ፣ እኔ ነካ ሲያደርጉት የሚፈርስ፣ እፍ ሲሉት ብን የሚል ከሆነ፣ እኔ የሚያዝ የሚጨበጥ የሌለው ሙልጭልጭ፣ እኔ መርህ- የለሽ  ልክስክስ፣ አከርካሪ የለሽ ልምጥምጥ ከሆነ እኛም የለንም። ድርጅት አይኖርም። ማኅበረሰብ መማቀቁ፣ ሀገር መውደሙ አይቀርም።  

እንደ ወያኔ ድርጅት በሚያጭበረብሩ መሪዎችና ተከታዮች የተገነባ ድርጅት በለስ ቀንቶት ወያኔን ቢያስወግድ የሚፈጥረው ሀገራዊና  መንግሥታዊ ሥርዓት የአጭበርባሪዎች ይሆናል። አድሎን፣ የድርጅትን ንብረት እንደራስ አድርጎ አለማየትን፣ ራስ ማስቀደምን፣ መስገብገብን፣ ወታደራዊ ፖሊስ ወይ ጓዶቼ አያዩኝም በሚል በጋራ ያጸደቁትን ሕግ ሥርዓትና ደንብ የሚጥሱ፣ ለጓዶቻቸው ደህንነትና ጤንነት የማይጨነቁ፣ እርስ በርስ  የማይፋቀሩ፣ የግል ድሎትንና ምቾትን ብቻ ማሰላሰልን ሥራዬ ብለው የያዙ አባላት የተሰባሰቡበት ድርጅት ታግሎ አታጋይ መሆን አይችልም።  እንደ ድርጅትም መዝለቅ አይችልም። ነጻ ወጥቶ ሌላውን ነጻ ማውጣት አይችልም። በአንድ ተአምር ወያኔን ማስወገድ ቢሳካለት ከወያኔ በላይ ሕዝብ አስመርሮ ወያኔ ማረኝ የሚል ዘመን እንዲመጣ ማድረጉ አይቀርም። በሀገራችን ታሪክ የሆነው ይህ ነው። ደርግን ያየ ሃይለስላሴ ማረኝ አለ። ወያኔን ያየ ደርግ ማረኝ አለ። እኛን ያየ ወያኔ ማረኝ የሚልበትን ሁኔታ ልንፈጥር አይደለም ትግል ውስጥ የገባነው። እኛ ትግል ውስጥ የገባነው መንግሥት ተቀይሮ መንግሥት በመጣ ቁጥር ካለፈው ሥርዓት አዲሱ እየባሰበት የሕዝብ ስቃይ የረዘመበትን የታሪክ ጉዞ ለመቅጨት ነው። እያንዳንዳችን ወደ ትግል የገባነው የሕዝብ እሮሮና ስቃይን ለአንዴና ለመጨረሻው እልባት ወይም መቋጫ ልናበጅለት ነው። ይህ ማድረግ የምንችለው በምንገነባው ድርጅት አማካይነት ነው። የምንገነባው ድርጅት የሚሰራው ከሲሚንቶና ከአሸዋ ወይም ከሌሎች ቁሳቁሶች አይደለም። በሰው ነው። በእኔ ነው። ሰው እንደሸክላ እንደ ብሎኬት ከአሸዋና ከሲሚንቶ የሚሰራ ወይም እንደ እንስሳ የምናራባው ፍጥረት አይደለም። ሰውን ሌላው ሰው አይሰራውም። ሰው ራሱን በራሱ ብቻ የሚሰራ ፍጥረት ነው። እኔ ፈቃደኛ ካልሆንኩ፣ ለመማር ዝግጁ ካልሆንኩ ሌላው ሰው ላስተምርህ፣ ልምከርህ ቢለኝ ዋጋ የለውም። 

ዛሬ እኔነታችንን ወደፊት ለማምጣት ለምንፈልገው ሀገራዊና ማኅበረሰባዊ ለውጥ እንዲመች አድርገን በሚገባ እዚሁ ካላነጽነው መጨረሻችን አሳፋሪ ውድቀት ነው። የሀገር እጣ፣ የ90 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን እጣ የሚወሰነው እዚህ እኛ መሃል እያንዳንዳችን በምንላበሰው ስብእና፣ በሚኖረን ሰብአዊ ሥነሥርዓትና ጥብቅነት፣ በምንገነባው የአብሮነትና የአንድነት ስሜት፣ በምንሸምተው እውቀትና ክህሎት ላይ ተመስረቶ ነው። እባብ ከሆነን የርግብ እንቁላል አንጥልም። የእባብ ፍልፈሎች እንጂ። ለዚህ ነው ከማናቸውም ጉዳዮች በላይ በግንቦት 7 ሕዝባዊ ኃይል ውስጥ እኔ ማነኝ ለሚለው ጥያቄ ቅድሚያ የሰጠነው። እኔ ማነኝ ወይም አንተ ማነህ ለሚለው ጥያቄ በጣም ቀላል ከሆኑ ነገሮች ተነስተን መልስ መስጠት እንችላለን። የእኔ ማነኝ ጥያቄ ምላሽ ግን እንደምናስበው ቀላል እንዳልሆነ ቀጥለን እንመለከታለን። 

Sunday 7 July 2013

የግብረ ሰዶማውያኑ ኑዛዜ በኢትዮጵያ

‹‹አዲስ አበባ ውስጥ ግብረ ሰዶማዊነት ተስፋፍቷል፡፡ በአንዳንድ ዩኒቨርሲቲዎችና የከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች፣ በየመንደሩ፣ በየሥርቻው፣ በየጓዳውና ጉድጓዳው ራሳቸውን ደብቀው ያደፈጡ ሁሉ ቢቆጠሩ ብዛታችን ያደላል፡፡ መጠሪያ ስማችን ጌይ ወይም ግብረ ሰዶማዊ የሚል ሳይሆን ‘ዜጋ’ የሚለው ነው፡፡ በዚህ ሕይወት ውስጥ ያልገቡ ሌሎች ወገኖችን ደግሞ ‹‹ቀጥ›› በሚል እንጠራቸዋለን፡፡››

ይህንን የተናገሩት ከሰባት እስከ 32 ዓመት ድረስ ሕይወታቸውን በግብረ ሰዶማዊነት ያሳለፉት ግብረ ሰዶማውያንና ግብረ ሰዶማውያት (ወንዶችና ሴቶች)፣ ‹‹ዝምታው ይሰበር ትውልድ ይዳን በእኛ ይብቃ›› በሚል ርዕስ በተዘጋጀ ዶክሜንተሪ ፊልም (ቪሲዲ) ውስጥ ባካሄዱት ቃለ መጠይቅ ላይ ነው፡፡

በቸርችል ሆቴል የስብሰባ አዳራሽ ውስጥ በተከናወነው ሥነ ሥርዓት ላይ ‹‹ስለኢትዮጵያ ዝም አንልም ግብረ ሰዶማዊነት በኢትዮጵያ የ666 አሠራር›› የሚል ታካይ ርእስ ባለውና ለምረቃ በበቃው በዚሁ ፊልም ውስጥ ይህንኑ ቃለ መጠይቅ ካካሄዱት ከእነዚህ ግብረ ሰዶማውያን ማብራሪያ ለመረዳት እንደተቻለው ሕጋዊና መደበኛ ሚስት አግብተው፣ ትዳር መስርተውና ልጆች ወልደው በሽምግልና ዕድሜያቸው ግብረ ሰዶም የሚፈጽሙ አዛውንቶች አሉ፡፡ አንዳንድ ጊዜ ‹‹አባባ መሽቷል እባክዎን ወደ ቤትዎ ሂዱ›› እያሉ ወጣት ግብረ ሰዶማውያን ይቀልዱባቸዋል፡፡ ይሳለቁባቸዋል፡፡ እነዚህም አዛውንቶች ታዋቂነታቸው በ‹‹ዜጎች›› ዘንድ ብቻ ስለሆነና በአካባቢያቸው ማኅበረሰብ ዘንድ የሚታወቁት ባለትዳርና የልጆች አባት ስለሆኑ ከማኅበረሰቡ ዘንድ እንዳይገለሉና ተከብረው እንዲኖሩ አድርጓቸዋል፡፡ 

የኢትዮጵያ ቡና ከዓለም ገበያ እየራቀ መሆኑ ሥጋት ፈጥሯል

የኢትዮጵያ ቡና ከዓለም አቀፍ ገበያ እየራቀ መጥቶ፣ ከነጭራሹ ሊወጣ የተቃረበበት ጊዜ ላይ እንደሚገኝ ለዘርፉ ቅርብ የሆኑ ተዋንያዎች የሚስማሙበት ሀቅ ነው፡፡ 
ኢትዮጵያ ለዓለም ቡናን ያበረከተች አገር ከመሆኗ ባሻገር እጅግ ተወዳጅ የሆነ ቡና የምታመርት አገር ናት፡፡ ዓለም አቀፍ የቡና ገዥዎች ይህንኑ የጣዕም ልዩነት በመረዳት የኢትዮጵያን ቡና ለመግዛት ከፍተኛ ፍላጎት ቢኖራቸውም፣ በቢሮክራሲ ውጥንቅጦች ምክንያት ቡናውን ማግኘት እንዳልቻሉ እየተናገሩ ነው፡፡ 
በቡና ግብይት ላይ ያለው ውጣ ውረድ ከፍተኛና ገዥዎች የማይተማመኑበት ደረጃ ላይ እየደረሰ በመሆኑ፣ በዓለም አቀፍ ገበያ በጣዕሙ ተወዳዳሪ የማይገኝለት የኢትዮጵያ ቡና ዋጋ እያጣ መምጣቱ የሚያስቆጭ ወቅታዊ ጉዳይ ሆኗል፡፡ የችግሩ ምንጮች በዋነኛነት የመንግሥት የቡና ግብይት አቀንቃኞቹ የንግድ ሚኒስቴርና የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ድርጅት እንደሆኑ የዘርፉ ተዋናዮች ያምናሉ፡፡ 
የቡና ግብይት ተዋናዮች እንደሚሉት፣ የችግሩ ምንጮች በእነዚህ ሁለት መንግሥታዊ ተቋማት የተወለዱ ችግሮች ናቸው፡፡ በመጀመሪያ የንግድ ሚኒስቴር የቡና ግብይት ዘርፍ የሥራ ኃላፊዎች የቡና ግብይት ሁኔታን በሚገባ አለመረዳታቸው ነው፡፡ በሁለተኛ ደረጃ የኢትዮጵያ ምርት ገበያ የሥራ ኃላፊዎች የግብይት ሁኔታውን ቢያውቁም፣ የመወሰን አቅም የሌላቸው በመሆኑ ነው፡፡ ‹‹እነዚህ አካላት ግን ያሉባቸውን የተወሰኑ ችግሮች ለማረም አልሞከሩም፤›› ይላሉ የተበሳጩት የቡና ግብይት ተዋናዮች፡፡ በምርት ገበያ በኩል አሉ ከሚባሉት ችግሮች መካከል አንዱ የቡና ልኬት (ሚዛን) ችግር ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ቀደም ባሉት ዓመታት በቡና ግዥ ሒደት የቡና ገለፋት በ20 በመቶ ታሳቢ ተደርጎ በግዥ ሒደት ቅናሽ ይደረግ ነበር፡፡ አሁን ባለው የምርት ገበያ የሽያጭ ሒደት ግን ቀድሞ የነበረው አሠራር እንዲቀር በመደረጉ፣ ቡና ከአቅራቢዎች ገዝተው የሚልኩ ኤክስፖርተሮች መቸገራቸውን ይገልጻሉ፡፡