Sunday 9 February 2020

ከአዲስ አበባ ፖሊስ ጀርባ ሆኖ በወጣቱ ነፍስ የሚቀልደው ማን ነው?

ከአዲስ አበባ ፖሊስ ጀርባ ሆኖ በወጣቱ ነፍስ የሚቀልደው ማን ነው?
«ዘውድአለም ታደሠ»
ባለፈው ከንቲባው «የአዲስ አበባን ፖሊስ እኛ ደሞዝ እንከፍለዋለን እንጂ እኛ አንመራውም» ብለው በምሬት ተናግረው ነበር።
የአዲስ አበባ ፖሊስ ከሊቅ እስከደቂቁ ህዝብን ከከተማው አስተዳደር ጋር ለማናከስ ተግቶ የሚሰራ ነው ሚመስለኝ። የከንቲባው ፅህፈት ቤት ሳያውቅ ከላይ ታዘን ነው በሚል የነእስክንድር ነጋን ስብሰባ በተደጋጋሚ ያቋርጣሉ። ባለፈው ቄራ አካባቢ እንደታየው ምንም ያላደረጉ ወጣቶችን አለአግባብ እየቀጠቀጡ ባደባባይ ይወስዳሉ። የአዲስ አበባ ትራፊክ ፖሊሶች አለአግባብ የከተማውን ሾፌሮች ለማማረር በሚመስል ሁኔታ ያንገላታሉ። ባለፈው አትክልት የሚያራግፍን ምስኪን ልጅ በጥይት ገደሉ። አሁን ደግሞ የከንቲባው ፅህፈት ቤት በማያውቅበት ሁኔታ በለሊት ሄደው ቤተክርስቲያን ለማፍረስ ሞከሩና አለአግባብ የሰው ነፍስ አጠፉ።
ይህ ሁሉ ሲሆን ህዝብ ድንጋይ አንስቶ የሚወረውረው ወደከተማ አስተዳደሩና ወደከንቲባው ነው። በህዝቡ አይፈረድም። ነገር ግን ነገሩን እንደኔ ጠንቅቆ ላየውና ባለፈው ከንቲባው የተናገሩትን በጥንቃቄ ለተመለከተ የአዲስ አበባን ህዝብና የከተማውን አስተዳደር ሊያባላ የሚሞክር ሃይል በአዲስ አበባ ፖሊስና በመንግስት መዋቅር ውስጥ እንደተሰገሰገ በቀላሉ ይገነዘባል። በዚህ ቀውጢ ሰአት ታከለ ኡማ ተጨማሪ ግርግር ናፍቆት ወጣቶች ላይ ተኩሱ ይላል ብሎ የሚያስብ ካለ ፖለቲካ አልገባውም።
ወዳጄ እንኳን እኔ አያቶቼም አዲስ አበባ ነው የተወለዱት። ታከለን ለመከላከል የወጣቶቹን ሞት ለማስተባበል የምሞክር ህሊና ቢስ እንዳልመስልህ። የአዲስ አበባ ልጅ እንኳን በጥይት በጥፊ እንዲመታ አልፈልግም። ነገር ግን ዛሬ ባይገባህም ነገ የምትረዳውን እውነት ልንገርህ ...
በየክልሉ ያለውን ጦርነትና ብጥብጥ ወደአዲስ አበባ በማምጣት አዲሳባን የጦርነት ማእከል ማድረግ የሚፈልግ ሃይል አለ። ይህ ሃይል በየግዜው በተቀናጀ ሁኔታ በከተማው አስተዳደር ላይ አሉባልታ በመንዛት የሸገርን ሰው ስጋት ላይ ጣለ። የተለያዩ ግርግሮች ለማስነሳት ሞከረ። መሬቶችን ሂዱና እጠሩ እያለ በመኪና እያስጫነ የማጠሪያ እንጨቶችን በራሱ ወጪ አቀረበ። የከተማ አስተዳደሩ ያንን በሃይል ለማስቆም ሲሞክር እንደዛሬው አይነት አደጋ እንዲከሰት ታቀደ። በተለያዩ የአዲስ አበባ ባዶ ቦታዎች መሬት በገፍ ወረረ። የከተማው አስተዳደር አፈርሳለሁ ሲል ይሄው ሃይል በሚዲያ መጥቶ የድሆችን ቤት አፍርሶ ሜዳ ላይ ሊጥላቸው ነው ብሎ አቧራ አስነሳ። ብቻ ምን አለፋችሁ የተለያዩ ግርግሮች በማስነሳት የአዲስ አበባ ሰው በቁጭት እንዲነሳ ነው እቅዱ። ግርግርና ጦርነቱን ከየክልሉ ጎትቶ መሃል አዲስ አበባ ማምጣት ነው እቅዱ። ከዚህ ውጪ የከተማው አስተዳደር ተጨማሪ ግርግርና ደም ማፍሰስ ናፍቆት የወጣቶችን ደም አፈሰሰ ብሎ ማሰብ እጅግ የተሳሳተ ድምዳሜ ነው።
የሸገር ሰው ሆይ መብትህን ጠይቅ። ኢ ፍትሃዊነት ስታይ ለምን? በል። ነገር ግን አደራህን በስሜት ተነሳስተህ ደምህን ለማንም እኩይ አጀንዳ አታፍስስ!! በመጠኑም ቢሆን ያለህን አንፃራዊ ሰላምና መረጋጋት ሊነጥቁህና ጦርነቱ ውስጥ ሊጨምሩህ ያሰፈሰፉ ሃይሎች አሉ። መብትህንና ነፃነትህን ለማንም አሳልፈህ አትስጥ። ነገር ግን ሁሉ በማስተዋል ይሁን። ላንተ ተቆርቀሪ መስሎ በየሚዲያው እንደጂምናስቲክ አስተማሪ “ተነስ ቁጭ በል” የሚልህ ሁሉ በነፍስህ ሊቆምር ነው የሚለፋው።
ዛሬ የከተማው አስተዳደር በፍጥነት ወደሚዲያ ወጥቶ መረጃ መስጠቱና ከንቲባውም የሟች ቤተሰቦች ቤት ድረስ በመሄድ ሃዘናቸውን መካፈላቸው ጥሩ ጅምር ነው። ከዚህ በተጨማሪ ግን የዚህ እኩይ ድርጊት ተሳታፊ የሆኑ አመራሮች ላይ ህጋዊ እርምጃ መውሰዱ እንደተጠበቀ ሆኖ በአስተዳደሩ ውስጥ ሆነው አስተዳደሩን ለማፍረስና ከህዝቡ ጋር በየእለቱ ለማጋጨት የሚሰሩ ሃይሎች እንዳሉ በብዙ ማስረጃዎች ስለታየ አስተዳደሩ ራሱን ያጥራ።
የአዲስ አበባ ፖሊስ ሙሉ በሙሉ ለአዲስ አበባ ህዝብ እንዲቆምና በአዲስ አበባ አስተዳደር በቀጥታ እንዲመራ ይደረግ። በየቀበሌው ያለ የአዲስ አበባ ወጣት ድጋፍ ከተሰጠው የራሱን ሰላም መጠበቅ የሚችል የሰለጠነ ነዋሪ ነውና ለአዲስ አበባ ወጣት ድጋፍ በማድረግ ወጣቱ አካባቢውን ከፖሊስ ጋር ሆኖ የሚጠብቅበት መንገድ ይመቻች። አደጋዎች ከመድረሳቸው በፊት የከተማው አስተዳደር መረጃ የሚያገኝበት social network ይዘርጋ። በተረፈ አለአግባብ ህይወታቸው ላለፈና በአስተዳደር ጉድለትም ሆነ በሌላ ምክኒያት ጉዳት ለደረሰባቸው ነዋሪዎች ተገቢው ካሳ ይከፈል።
በተረፈ ከንጉሱ ጀምሮ መሬት ላራሹ ሲል ላለቀው፣ በደርግ ቀይ ሽብር ነጭ ሽብር እየተባለ ለተገደለው፣ በኢህአዴግ ከአንድም ሁለት ሶስቴ በጅምላ ለተረሸነው የአዲስ አበባ ህዝብ ከዚህ በኋላ ሞት አይገባውምና በከፍተኛ ሁኔታ ጥንቃቄና ጥብቅ ቁጥጥር ይደረግ። በተጨማሪም የከተማውን አስተዳደርም ሆነ የፌደራል መንግስቱን ፖለቲካዊና ሃይማኖታዊ በሚመስሉ አጀንዳዎች ተከልሎ የመንግስትን እጅ ለመጠምዘዝ የሚሞክሩ ሰዎችን ያለምን ማመንታት ህጋዊ እርምጃ ይወሰድ። ህዝብ ከሁሉም በፊት ሰላምና ደህንነቱ ተጠብቆ መኖር ነውና ሚፈልገው ከዚህ በኋላ መንግስት ሰላምን በአስተማማኝ ሁኔታ ያረጋግጥ!!
ለሟች ቤተሰቦች ፈጣሪ መፅናናትን ይስጥልን!!