Saturday 28 April 2018

የስኳር በሽታን የሚያድን መድሀኒት ያገኘ ኢትዮጵያዊ ሀኪም


``ቡና እግዚአብሔር እጃችን ላይ ያስቀመጠልን አልማዝ ነው``


ዶ/ር ፈንታሁን አበበ ትውልድና ዕድገታቸው በሰሜን ሸዋ መስተዳድር ዞን ሸዋሮቢት ከተማ ነው:: የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን እንዳጠናቀቁ በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ በሒሳብ መዝገብ አያያዝ (አካውንቲንግ) ዲፕሎማ እና በአስተዳደር ጥበብ (ማኔጅመንት) በመጀመሪያ ዲግሪ ተከታትለዋል:: በመቀጠልም ወደ አዲስ አበባ አቅንተው የጥርስ ሕክምና ትምህርት (ዶክተር ኦፍ ዴንታል ሜዲስን) አጥንተዋል:: በአሁኑ ወቅትም አዲስ አበባ በሚገኘው የስኳር ሕሙማን ማዕከል ሕክምና ይሰጣሉ፤ በአፍሪካ ሜዲካል ኮሌጅ የጥርስ ሕክምና ትምህርት እና የጥናትና ምርምር ክፍሎች ኃላፊና መምህር ናቸው::

ዶክተር ፋንታሁን የሕክምና ትምህርታቸውን ከጀመሩበት ጊዜ አንስቶ ወደ ምርምር ሥራው በማዘንበል አስደናቂ የሆኑ ግኝቶችን ይፋ አድርገዋል፤ በሀገር አቀፍና ዓለም ዓቀፍ ደረጃም ዕውቅና ተችሯቸዋል:: የአየር ብክለትን ለመቆጣጠር የሚያስችል ግኝት አበርክተው ዓለም ዓቀፍ ዕውቅና አግኝተዋል:: ዝናብን በሰው ሰራሽ መንገድ በፈለጉት ቦታ ላይ ማዝነብ እንደሚቻልም በጥናት ደርሸበታለሁ ብለው በፈጠራ አስመዝግበዋል:: በተለይ የዓለማችን የጤና ችግር የሆነውን የስኳር በሽታም አክሞ ማዳን እንደሚቻል አረጋግጫለሁ ብለዋል:: ዶክተር ፋንታሁንን የበኲር እንግዳችን አድርገን በስኳር በሽታ መድኃኒት ዙሪያ “አዲስ ግኝት አለኝ” ባሉት ዙሪያ እንነጋገራለን፤ መልካም ንባብ!

ዶክተር ፋንታሁን ከመጀመሪያ የማኅበራዊ ሳይንስ ምሩቅ ሆነው እንዴት ወደ ጤናው ዘርፍ መሸጋገር ቻሉ?

ዝንባሌውና ቁርጠኝነቱ ካለ ይቻላል፤ የማይቻል ነገር አይደለም:: እንዳልከው ከመጀመሪያ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም የገባሁት በማኅበራዊ ሳይንስ ዘርፍ ነው:: አንደኛው ምክንያት የ2ኛ ደረጃ ትምህርት ማጠናቀቂያ ፈተናን ስሠራ “ሌሎችን ለማገዝ” በሚል የተሳሳተ አካሄድ ተረጋግቼ ባለመሥራቴ ውጤቴ ዝቅ በማለቱ የተነሳ ነው:: ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የቤተሰብ ፍላጎትና የመንግሥት የተማሪ አመዳደብ ሁኔታ ነው፤ በእነዚህ ምክንያቶች የተነሳ የማኅበራዊ ሳይንስን ተቀላቀልኩ:: በዚያው ግን አልቀረሁም፤ በኋላ ላይ ዝንባሌዬ ወደሆነው የሕክምናው ዘርፍ በግሌ ገብቼ ተማርኩ::

ወደ ምርምር ሥራ የገቡት መቼ ነው? የሕክምና ትምህርቱን ከጨረሱ በኋላ ወይስ ሳይጨርሱ ነው?

የህክምና ትምህርቱን ገና በመማር ላይ እያለሁ ነው:: በትምህርት ላይ እያለን ለተግባር ልምምድ በአዲስ አበባ ከተማ በሚገኙት ጳውሎስ፣ ምኒልክ፣ ዘውዲቱ፣ … ሆስፒታሎች እንሄድ ነበር:: በዚያን ጊዜ የተመለከትኳቸው አንዳንድ ነገሮች ገፋፉኝና ወደ ምርምሩ መግባት ጀመርኩ:: በተለይ የስኳር ታማሚዎች የሚያዩት ፈተና ከባድ ነው፤ ከሚወስዱት መድኃኒት ጋር ተያይዞም የሚያጋጥማቸው ውስብስብ ችግር አለ:: ከዚያ በመነሳት ነው የስኳር በሽታ መድኃኒት ላይ ምርምር ማድረግ የጀመርኩት::

የስኳር በሽታ በጣም አስቸጋሪ ነው፤ ታማሚዎቹ ሌላ በሽታ ሲያማቸው እንኳ ታክመው ለመዳን የሚገጥማቸው ችግር በጣም ከባድ ነው:: የታማሚዎቹ ቁጥር ደግሞ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ነው፤ በዓለም ላይ ከ400 ሚሊዮን በላይ ሰዎች የስኳር ታማሚ ናቸው:: በኢትዮጵያም ቁጥሩ በጣም እያሻቀበ ነው፤ በተለይ ደግሞ ታዳጊ ሕጻናት በበሽታው ክፉኛ እየተጠቁ ነው:: ወላጆች የልጆቻቸውን የስኳር መጠን በየቀኑ እየለኩ የሚከታተሉበት ደረጃ ላይ ደርሰዋል፤ በዚያ ላይ ልጃቸውን በሽታው እንዳይነጥቃቸው ወላጆች በስስት ሲመለከቷቸው ስታይ በጣም ያሳስብሃል:: በዚህ ተነስቼ ነው እንግዲህ ወደ ምርምሩ የገባሁት::

የስኳር በሽታ መድኃኒትን “ከቡና አግኝቻለሁ” እያሉ ነው፤ ቡናን ለምርምር እንዴት መረጡት?

ቡና ለኢትዮጵያውያን ምልክታችን ነው፤ እኔ ከልጅነቴም ሳድግ ቡና ሲጠጣና ዘመድ ሲሰባሰብ ከማዬት ባለፈ ጧት ጧት “የገቢ ምንጫችን ቡና ቡና፣ የኢኮኖሚ ዋልታ ቡና ቡና …” እየተባለ በራዲዮ ሲዘመር እየሰማሁ ነው ያደግሁት:: ይህ እንዳለ ሆኖ ደግሞ በተለይ ታዳጊ ሀገራት ባለን ሀብት እንዳንጠቀም የሚደረግብን ተፅዕኖ በጣም ይሰማኛል:: ከዚህም በላይ ከፍተኛ የመሬት ሽፋን የያዘው ቡና ነው፤ ከ25 ሚሊዮን በላይ የኢትዮጵያ ሕዝብም በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ በቡና የሚተዳደር ነው:: በዚያ ላይ መንግሥት ባሉን የግብርና ምርቶች ላይ እሴት መጨመርን በእጅጉ ያበረታታል:: ከዚህ በመነሳት ‘ቡና ላይ ምን ዓይነት እሴት መጨመር አለብን?’ ብዬ ነው ቡና ላይ ለማጥናት የተነሳሁት::

ለረዥም ዓመታት ኢኮኖሚያችንን የደገፈውን ቡና እሴት መጨመር በጣም አስፈላጊ እንደሆነ በፅኑ ካመንኩበት በኋላ ደግሞ ይበልጥ ያነሳሳኝ ምክንያት አለ:: በበለፀጉ ሀገራት የሚኖሩ ድርጅቶች የኛን ቡና፡- ‘የይርጋ ጨፌ፣ የሲዳማ፣ … ቡና የኛ ነው’ ማለት መጀመራቸው በጣም አነሳሳኝ:: “ስታር ባክስ” ከእኛ ሀገር በላይ በኛ ቡና ላይ ተጠቃሚ ሲሆን ስመለከት በቡናችን እንደ ባለቤት በመጠበብ የሆነ ነገር መሥራት አለብን ብዬ ማጥናት ጀመርኩ::

ያጠኑት ቡናን ብቻ ነው ወይስ የለዩት ሌላ ዘርፍ ነበር?

ለማጥናት የለየኋቸው ዘርፎች ነበሩ፤ የጤና ባለሙያ ስለሆንኩ ጤናውንም ምጣኔ ሀብቱንም ታሳቢ አድርጌ ነው:: ከምጣኔ ሀብት አኳያ በተለይ ከድርቅ ጋር በተያያዘ የውኃ ማማ የሆነች ሀገር ይዘን በመጠማታችን ማጥናት ፈለግሁ:: ከጤና አኳያ ደግሞ ቀደም ሲል ያነሳሁትን የስኳር በሽታ መፍትሔ መፈለግ አሰብኩ:: ከምጣኔ ሀብት አኳያ ቡናን ለማጥናት እንቅስቃሴ ስጀምር የያዛቸውን ንጥረ ነገሮች አስቀድሜ ማወቅ ፈለግሁ:: የሚገርመው ነገር ቡና ለብዙ በሽታዎች ፈውስ የሚያገለግሉ መድኃኒቶች መቀመሚያ ንጥረ ነገሮችን ይዞ አገኘሁት::

በቡና ውስጥ ከ13 በላይ የመድኃኒት መሥሪያ ንጥረ ነገሮች ይገኛሉ:: ከእነዚህ ውስጥ አንዱ በሳይንሱ ‘ክሎሮጀኒክ’ የሚባለው ነው:: ክሎሮጄኒክ ደግሞ የሰውን የደም ውስጥ የስኳር መጠን የሚያመጣጥን ንጥረ ነገር ነው:: ስለዚህ “ከሀገራችን ቡና ይህ ንጥረ ነገር ከተገኘ ስኳርን ማከም ይቻላል” ብዬ ገመትኩና ወደ ጥናቱ ገባሁ:: ይህም እግረ መንገዴን የስኳር በሽታ መድኃኒትን ከቡና ስፈልግ በቡና ላይ እሴት ጨምሬ ከፍተኛ ገቢም እንድናገኝበት ለማድረግ ያግዘኛል ብዬ ወደ ጥናቱ በጥልቀት ገባሁበት::

ግኝቱን እንዴት አረጋገጡት?

መጀመሪያ በንድፈ ሀሳብ ደረጃ ከተጠናና ከታወቀ በኋላ መጀመሪያ በእንስሳት ላይ ነው የሚሞከረው:: በእንስሳት ላይም “እንዴት መሞከር አለበት?” የሚለውን ከኢትዮጵያ የመድኃኒትና ምግብ ቁጥጥር ባለስልጣን በሚገኘው ቤተ-ሙከራ (ላቦራቶሪ) ሄጄ “ክሎሮጀኒክ አለኝ፤ ለስኳር ታማሚዎች የስኳር መጠናቸውን የሚያስተካክልና ጣፊያ ‘ኢንሱሊን’ የተባለውን ሆርሞን ማመንጨት እንዲችል የሚደርግ ነው:: ሰዎች ዕድሜ ልክ ከሚወስዱት ክኒን ወይም መርፌ የሚገላግል፣ በሽታውን ማዳን የሚችል ነው” አልኳቸው::

እነሱም (የኢትዮጵያ የመድኃኒትና ምግብ ቁጥጥር ባለስልጣን ኃላፊዎች) ተቀብለውኝ በራሳቸው ቤተ ሙከራና በአይጦች ላይ ሞክረውት ከጎንዮሽ ጉዳትና ከመርዛማነት ነፃ መሆኑን አረጋግጠው ሰጡኝ:: በመቀጠልም ከአካባቢ ጤናና ቁጥጥርም በተመሳሳይ መልኩ ማረጋገጫ አሠራሁ:: በተጨማሪም ቡና ዘወትር የምንጠጣው ተፈጥሯዊ ፍሬ በመሆኑ የሚወሰደው መድኃኒትም ሌላ ባዕድ ነገር ሳይጨመርበት ከእርሱ በቀመር የሚወሰድ ንጥረ ነገር በመሆኑ ችግር የሌለበት ስለሆነ ምግብ እንደማለት ነው::

ስለዚህ በቀመር የወሰድኩትን ንጥረ ነገር ከሚመለከታቸው አካላት መረጋገጫ ካገኘሁ በኋላ ፈቃደኛ ለሆኑ የስኳር ታካሚዎች ሰጠኋቸው:: መድኃኒቱን የወሰዱት ሰዎችም የሚገርም ለውጥ አገኙ፤ አሁን ላይ በመዳናቸው ኢንሱሊን በመርፌ በየቀኑ ይወስዱ የነበሩ ሰዎች አቋርጠውታል::

ከቡና የስኳር መድኃኒት ከተገኘ ቡና በመጠጣት መፈወስ ያልተቻለው ለምንድን ነው?

ፈዋሹ ነገር ከቡና ተገኘ እንጅ ቡናው እንዳለ ሲወሰድ ፈዋሽ አይደለም:: ንጥረ ነገሩ በተለየ ቀመር ወጥቶ ነው ጥቅም ላይ የሚውለው:: ለዚህ ተግባር የሚውለውም የተቆላው ቡና ሳይሆን በጥሬው ያለው ነው:: እርሱም ቢሆን በተለየ ቀመር የሚፈለገው “ክሎሮጀኒክ” መውጣት አለበት:: ቡናው ሲቆላ በጣም እንዲያር ስለሚደረግ ብዙ ጠቃሚ ነገሮቹን ያጣል፤ ቡና ሲጠጣም ነጣ ብሎ መቆላት እንዳለበት በዚሁ አጋጣሚ ለመናገር እወዳለሁ::

በእርግጥ በቡና ውስጥ ብዙ ፈዋሽነት ያላቸው ንጥረ ነገሮች አሉ:: ለምሳሌ ያመረቀዘ ቁስል ላይ ቡናውን ደቀቅ አድርጎ ቢደመድሙበት ያድናል:: ካንሰር ያለበትን ሁሉ ቁስለቱን በቀላሉ ያድነዋል፤ የመድኃኒት መላመድ ችግር ለገጠማቸው ሰዎችም አጋዥ የሆኑ ንጥረ ነገሮችን የያዘ ነው:: በእርግጥ አንዳንዶች የጎንዮሽ ጉዳት እንዳለው ይናገራሉ፤ እኔ ግን “ምንም ነገር ቢሆን መጠኑን ካለፈ ስለሚጎዳ እንጅ ቡና ጎጂ ስለሆነ አይደለም” ብዬ ነው የማምነው:: ካልበዛ ለምግብ እንሽርሽሪት በጣም ጠቃሚ ነው፤ ችግሩ እኛ ቡናን አሳርረን ስለምንቆላው ወደ ካርቦንነት ይቀየርና በደም ውስጥ ከኦክስጅን ጋር ተዋሕዶ ካርቦን አንድ ኦክሳይድ (ካርቦንሞኖኦክሳይድ) ስለሚፈጥር የመተንፈስና የልብ መምታት ችግር ሊያመጣ ስለሚችል ነው::

ቡናን ለመድኃኒት መቀመሚያነት መጠቀሙ ምን ያህል ምጣኔ ሀብታዊ ጠቀሜታ አለው?

በእርግጥ ያደጉት ሀገራት ያለንን ሀብት እንድንጠቀም አይፈልጉም እንጅ ቡና እግዚአብሔር እጃችን ላይ ያስቀመጠልን አልማዝ ነው:: ቡና ለብዙ መድኃኒት መቀመሚያነት መዋል የሚችል ሳንቆፍር የምናገኘው ሀብታችን ነው:: አሁን ባለው ነባራዊ ሁኔታ ቡናን በጣም ርካሽ በሆነ ዋጋ ነው ለዓለም እያቀረብን ያለነው:: በእኔ ግኝት መሠረት ግን የአንዷ ቡና ፍሬ ግማሽ የአንድ ክኒን መስሪያ የሚሆን ንጥረ ነገር ይዛለች::

ይህ ማለት አንድ ሰው የሚወስደው ሙሉ ይዘት 21 ፍሬ ክኒን ቢሆን ለዚህ የሚያስፈልገው 11 ፍሬ ቡና ነው እንደማለት ነው:: በዚህ ስሌት መድኃኒቱን በሙሉ አቅም ወደማምረት ብንገባ አንድ ኩንታል ቡና በሚሊዮኖች የሚቆጠር ብር ያሳፍሰናል ማለት ነው:: ለአንዳንዶች ይህ የተጋነነ ይመስላቸዋል፤ ግን ሀቅ ነው:: አጥንተው ማረጋገጥ ይችላሉ::

ምን ያህል ታካሚዎችን መፈወስ ችለዋል?

በዚህ ወቅት (ሕዳር 2009ዓ.ም የመጀመሪያ ሳምንት) ከ500 በላይ ሰዎች መድኃኒቱን እየወሰዱ ናቸው፤ ከእነዚህ ውስጥ ከ400 በላዩ ከመርፌና ክኒን ተገላግለዋል::ይህን የማደርገው በራሴ ጥረት በግሌ አዲስ አበባ ስታዲዬም አካባቢ በተከራየሁት ቤት ፈቃድ አውጥቼ እየሠራሁ ነው::ይሁንና የመሥሪያ ቦታና የገንዘብ እገዛ ባለማግኘቴ በወረፋ ችግር በየቀኑ ከ60 በላይ ሰው ሳይስተናገድ ይመለሳል:: በቂ የሆነ የቤተ ሙከራና ሕክምና መስጫ ክፍል ስለሌለኝ::

የስኳር በሽታ የተለያየ ዓይነት ስለሆነ እርሶ ማዳን የቻሉት የትኛውን ነው?

እንዳልከው የስኳር በሽታ ዓይነት አንድ እና ዓይነት ሁለት የሚባል አለው:: እኔ ማዳን የቻልኩት ሁለቱንም ነው::

የተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን የስኳር በሽታ መድኃኒት ማግኘትዎን ሲያስተባብሉ ነበር፤ ምክንያቱ ምንድን ነው?

ይህንን የምርምር ይዘትና ውጤት ይዤ ስቀርብ በተደጋጋሚ የቀረቡብኝ አሉታዊ ትችቶች አሉ፤ አንዳንዶቹ “እንዴት ዓለም ዓቀፍ ችግር ለሆነና ፈረንጅ መፍትሔ ላጣለት የስኳር በሽታ ኢትዮጵያዊ ለዚያውም ከቡና መድኃኒት ሊያገኝ ይችላል?” ብለው በጭፍን ይወርዱብኛል:: በሙያው ውስጥ ያሉና አዋቂ የምላቸው ሰዎች ጭምር ስልክ እየደወሉ አጣጥለውኛል:: ግን ዓላማ ስላለኝና ፍንጭም ያየሁበት ስለሆነ ቀጥዬበት ከዚህ ደርሻለሁ:: ሌሎቹ “ለዚያውም ከኢትዮጵያ ቡና¡” ብለው በመሳለቅ በሕክምና መጽሔቶች ሳይቀር ጽፈውብኛል:: ግን ጠጋ ብለው በዕውቀት ዓይን ቡናችንን ቢያዩት ትልቅ ክብር የሚሰጡት ይመስለኛል:: በሩቁ ባንገዳደል ጥሩ ነበር፤ ማበረታታት ልምዳችን ቢሆን መልካም ነበር:: እንዲያውም ፈቃድ የሰጠኝ አካል ሁሉ ፈቃድ እንዳልሰጠኝ ተደርጎ ሁሉ ተዘግቧል:: በኋላ ሄጄ ምን እያላችሁ ነው? ስላቸው “እንዲያውም አንተን ማገዝና ማበረታታት ነው የምንፈልገው” ብለው ባለሙያዎችን ሁሉ መደቡልኝ፤ ድጋፍም እያደረጉልኝ ነው:: ግን በወቅቱ ሆን ብለው የዘመቱብኝ ሰዎች ክፉኛ ስሜቴን ጎድተውታል:: እንዲያውም ልዩ እገዛ ነበር የሚያስፈልገኝ:: የሚገርመው ግን ሙያዊ እና በዕውቀት ተመሥርቶ ተቃውሞ የሚያቀርቡ ሰዎች አለመኖራቸው ነው::

ቡናችን አካባቢያዊ የሆነ ስያሜና ዝርያ አለው፤ የስኳር ፈዋሽ ንጥረ ነገር ይዘቱ በዚያው ልክ ይለያያል?

ቡናዎቹ እንደ መልክአ ምድራቸው በጣዕምም በንጥረ ነገር ይዘትም ይለያያሉ፤ ቡና የሚያሰኛቸው መሠረታዊ ባሕሪ እንዳለ ሆኖ:: አንዳንዶቹ የቡና ዛፎች እንደ ሙጫ ሌሎቹ ደግሞ እንደ ወይን ያለ ፈሳሽ አላቸው:: ይህ ነገር በሚይዙት ንጥረ ነገር ላይም ስለሚንፀባረቅ ሁሉም ቡናዎቻችን የስኳር ፈዋሽ ንጥረ ነገሩን ይዘዋል፤ በመጠን ግን ይለያያሉ::

አሁን ላይ በዓለም እየተሰጠ ያለው የስኳር በሽታ መድኃኒት ዕድሜ ልክ የሚወሰድ ነው፤ የእርሶ ግኝትስ?

በዓለም ላይ ጥቅም እየሰጡ ያሉት የስኳር መድኃኒቶች እንዳልከው በመርፌ ወይም በክኒን መልክ ሆነው ዕድሜ ልክ የሚወሰዱ ናቸው:: ያ መሆኑ ደግሞ የምጣኔ ሀብት፣ የስነ-ልቦና፣ የጤና ችግር አለው፤ አማራጭ ስለሌለ የሚወሰድ መድኃኒት ነው ማለት ይቻላል:: በእኔ እምነትና ባገኘሁት ውጤት ግን የስኳር በሽታ ታክሞ መዳን የሚችል ነው፤ ዕድሜ ልክ መድኃኒት መውሰድ አያስፈልግም:: በእኔ ግኝት መሠረት ለተወሰነ ጊዜ መድኃኒቱን ወስደው ዘላቂ ፈውስ ያገኛሉ::

ከመንግሥት አካልስ ምን ያህል ድጋፍ እያገኙ ነው?

መጀመሪያ ላይ በዚያም አካባቢ ውዥንብሮች ነበሩ:: በተለይ የስኳር በሽታ መድኃኒት በየጊዜው የሚገዟቸው ሰዎች ህመምተኞች የእኔን መድኃኒት ወስደው ሲድኑና ሲያቋርጡ ይበሳጩ ነበር፤ በግልፅ “እንዴት ይድናሉ!” ብለው የተበሳጩ ሰዎች አጋጥመውኛል:: አሁን ላይ ግን “ምን እናግዝህ? ባለሙያዎችን አቋቁመን እንዲረዱህ ማድረግ እንፈልጋለን?” እያሉኝ ነው፤ በተለይ ከመድኃኒትና ምግብ ቁጥጥር ባለስልጣን ጥሩ ድጋፍ እያገኘሁ ነው::

Wednesday 25 April 2018

የሙሴ + አሮንና ሖር = ድል



በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከሚገኙ የመሪና የተባባሪ ድርሻን ከሚገልጡ ታሪኮች አንዱ የሙሴና፣ የአሮንና የሖር ታሪክ ነው(ዘጸ. 17÷8-16)፡፡
አማሌቃውያን ከእስራኤል ጋር ሲዋጉ ኢያሱ ጎልማሶቹን ይዞ ከአማሌቃውያን ጋር ይዋጋ ነበር፡፡ ሙሴ ደግሞ ወደ ኮረብታው ወጣ፡፡ ሙዜ እጁን ባነሣ ጊዜ እስራኤል ድል ያደርጋሉ፡፡ ሙሴ ደክሞት እጁን ባወረደ ጊዜ ደግሞ አማሌቅ ድል ያደርጋሉ፡፡ በዚህ ሁኔታ ሙሴ ቀኑን ሙሉ ዋለ፡፡ በመጨረሻ ግን የሙሴ እጆች ከበዱ(ደከሙ)፡፡ ይህን የተመለከቱት አሮንና ሖር ለሙሴ የድንጋይ ወንበር አዘጋጁለት፤ ሙሴም እዚያ ድንጋይ ላይ ተቀምጦ እጁን ዘረጋ፡፡ ድሉም ለእስራኤል ሆነ፡፡ ነገር ግን አሁንም ሙሴ እጆቹ እየደከሙ መጡ፡፡ አሮንና ሖርም በግራና በቀኝ ሆነው የሙሴን እጆች ከፍ አድርገው ደገፏቸው፡፡ ያን ጊዜ ሙሴ እጆቹን አነሣ፡፡ እስራኤልም አማሌቅን ፈጽመው ድል አደረጉ፡፡
አንድ መሪ ውጤታማ የሚሆው ብቻውን አይደለም፡፡ እንኳንና በሰዎች የተመረጠ መሪ እግዚአብሔር የመረጠው ሙሴ እንኳን ብቻውን ውጤታማ መሆን አልቻለም፡፡ መሪ ምን ጠቢብ፣ ጎበዝ፣ ውጤታማ፣ ተወዳጅና ዐቅም ያለው ቢሆንም እንኳን እንደ ሙሴ እጆች መዛሉ አይቀሬ ነው፡፡ ስለዚህም እንደ አሮንና እንደ ሖር መንገዱን አይቶ የሚደግፈው ይፈልጋል፡፡ መልካም መሪ ውሳኔዎቹ፣ የለውጥ ሐሳቦቹ፣ ዕቅዶቹና ቃል ኪዳኖቹ ተግባራዊ እንዲሆኑ የሚያበረቱት አሮንና ሖር ይፈልጋል፡፡ አሮንና ሖር ለሙሴ የተሰጠው አልተሰጣቸውም፡፡ ነገር ግን ሙሴን ደግፈው የሚፈልጉትን ውጤት አመጡ፡፡ ሁሉም ሰው መሪ ባይሆንም የመልካም መሪን ሐሳብ፣ ዕቅድ፣ ራእይና ውሳኔ በመደገፍ ግን ለውጥ ማምጣት ይቻላል፡፡
ሁሉም ሰው ደራሲ ባይሆንም የደራሲውን እጆች መደገፍ ግን ይችላል፡፤ ሁሉም ሰው ተመራማሪ ባይሆንም የተመራማሪውን እጆች ግን መደገፍ ይችላል፡፡ ሁሉም ሰው የበጎ አድራጎት ማኅበር መመሥረት ባይችልም የበጎ አድራጎት ማኅበራቱን እጆች መደገፍ ግን ይገባል፡፡ ሁሉም ሰው የፖለቲካ ፓርቲ መመሥረት አይገባውም፡፡ የፓርቲዎቹን እጆች መደገፍ ግን ይቻላል፡፡ ሁሉም ሰው ሐሳብ ላያመነጭ ይችላል፡፡ የሐሳብ አመንጭዎችን እጆች ግን መደገፍ ይገባል፡፡ ሁሉም ሰው ታጋይ ላይሆን ይችላል፤ የታጋዮችን እጆች መደገፍ ግን ይገባል፡፡
ሙሴ አንድ ደጋፊዎቹ ግን ሁለት ነበሩ፡፡ ምንጊዜም ከደጋፊዎች ተደጋፊዎች ያንሳሉ፡፡ ታሪክ እንደሚያስተምረን ዓለምን የለወጧት ጥቂት ባለ ተሰጥዖዎች ናቸው፡፡ ነገር ግን ሐሳባቸውን፣ መንገዳቸውን፣ ድርሰታቸውን፣ ምርምራቸውን፣ ሙከራቸውን፣ አመራራቸውን፣ ትምህርታቸውን፣ ጥረታቸውን የሚደግፉ ተቋማት፣ ግለሰቦች፣ ሚዲያዎች፣ መንግሥታትና ማኅበረሰቦች በማግኘታቸው ውጤታማዎች ሆኑ፡፡
ብዙ ሙሴዎች አሮንና ሖርን አጥተው እጃቸው ዝሎ ድል ሆነዋል፡፡ መንገዱ፣ ሐሳቡ፣ ውጣ ውረዱ፣ ሙግቱ፣ ጭቅጭቁ፣ የሰው ትችትና ወቀሳ፣ ስድብና ዕንቅፋትነት አዝሏቸው ድል ከማድረግ ድል ወደመሆን ወርደዋል፡፡ ክብሪቱን የሚያግዙት እንጨቶች ጠፍተው ቦግ ብሎ ጠፍቷል፡፡ በታሪካችን ብዙ ሙሴዎች መጥተው ነበር፡፡ ነገር ግን የሚያግዛቸውና ክንዶቻቸውን የሚደግፍ፤ ቢያንስ የድንጋይ መቀመጫ እንኳ የሚሰጥ አጥተው በሞትና በሽፈት ድል እየሆኑ ተገቢውን ለውጥ ሳያመጡ ቀርተዋል፡፡
ድል የማድረጊያ አንዱ መንገድ ብርቱዎቹን መደገፍ ነው፤ ክንዳቸው፣ ድምጻቸው፣ ሥራቸው፣ ጥረታቸው፣ ሐሳባቸው፣ ትግላቸው፣ ከፍ ሲል ድል የሚያደርጉትን መደገፍ ነው፡፡ መጥፎ ሠሪዎችን ከምንቃወመው በላይ መልካም ሠሪዎችን የማንደግፍ ከሆነ ውጤት አናመጣም፡፡
የሙሴም ታላቅነት ምን መሪ፣ እጆቹ ታላቅ ሥራ የሚሠሩና ድል አድራጊ ቢሆንም ሊደክም፣ ሊሸነፍ፣ ሊያቅተውና ሊዝል እንደሚችል አመነ፡፡ ያለ ሌሎች ድግፋ ብቻውን ለውጥ እንደማያመጣ ተቀበለ፡፡ ታላቅነት ማለት የታናናሾችን አስተዋጽዖ መናቅ አይደለም፡፡ ሁሉን ብቻዬን አደርገዋለሁ አላለም፡፡ አሮንና ሖር እንደሚያስፈልጉት ተቀበለ፡፡ ጎበዝ ሰው እንዲህ ነው፡፡ ሁሉንም ለብቻዬ እችለዋለሁ አይልም፡፡ የአንድ ሰው ውጤታማነት የብዙ ሰዎች አስተዋጽዖ ውጤት ነውና፡፡ ድል የሙሴም፣ የአሮንና የሖርም የየብቻ ውጤት አይደለም፡፡ ድል የሙሴ፣ የአሮንና የሖር የኅብረት ውጤት ነው፡፡

Wednesday 11 April 2018

ሰጋጅና አሰጋጅ !


Image may contain: 1 person, sitting




ቴዎድሮስ ተ/አረጋይ

ይህ ፎቶ በፎቶ ሾፕ የተቀናበረ አይደለም ብዬ ልመን ። እውነት ነው ብለን ካመንን ፣ ተንበርካኪው " ጋዜጠኛ " ከሆነ ስራውን ትቶ ለመስገድና ለማጎብደድ የሚመች ሌላ ስራ ቢፈልግ ያዋጣዋል ። የሙያ ፍቅር ወይም የቦታው አለመመቸት ሊባል መቸው አይችልም ። በዘመኑ ቋንቋ ተንበርካኪነት ነው ። ሰውየው ራሱን ብቻ ሳይሆን የጋዜጠኛን ሁሉ ክብር ይዞ ነው የተንበረከከው ። ከሰጋጁ ደግሞ አሰጋጁ ይደንቃል ። አጠገቡ ሌላው ቢቀር አንደ የሰው ልጅ ተንበርክኮ ( በፈቃዱም ይሁን በምንም ምክንያት ) እንዲህ ተደላድሎ ማውራት መቻሉ ይገርማል ።

ሰውን ለመርገጥም መቻልን ይጠይቃል ። ማንም ድንገት ተነስቶ እንደ ሁለቱም ሰዎች መሆን አይችልም ። ይህ ሙያ የእኔ ሙያ ነው ። የጋዜጠኝነት ሙያ የሕይወት መስዋዕትነት የሚጠይቅ ሙያ መሆኑን አውቃለሁ ። ምንም ሳይቸግር እንዲህ መሆን ግን ክብረ ነክ ነው ። ለሕዝቦች እኩልነት ፣ ለፍትህ ፣ ለዴሞክራሲ በረሀ ግብቶ የታሀለ ሰው ከምቾት በኋላ እንዲህ ሲሆን ማየት ብዙ ጥያቄ ያስነሳል ። ጉዳዩ በዚህ ብቻ አያበቃም ። በአንዲት ነጻና ሉዓላዊት ሀገር ፣ ያውም ለሌላ መስገድን ለማታውቅ ሀገር ይህን ትርዒት ማየት አስደማሚ ነው ። ይሁንና ሁለቱም ሰዎች በአንድ ያልታወቀ ምክንያት ተስማምተዋል ። ይህ ችግር ሳይሆን ስምምነት ነው ።



Wednesday 4 April 2018

የዐቢይ ንግግር ሰባት አዕማድ



የሀገሬ ሰው ‹ካልተናገረ አይታይ ብልሃቱ፣ ካልታረደ ዓይታይ ስባቱ› ይላል፡፡ ንግግር የሰው ልጅ ከተሰጡት የላቁ ጸጋዎች አንዱ ነው፡፡ ንግግር ሰዎችን ሊያግባባቸው፣ ወደ አንድነትና ኅብረት ሊያመጣቸው፣ ሊያከራክራቸውና ሊያወያያቸው ኃይል አለው፡፡ ከመሪዎች ከሚጠበቁ ነገሮች አንዱ ኃይል ያለው ንግግር ነው፡፡ ኃይል ያለው ንግግር በሚመርጣቸው ቃላት፣ በሚጠቀምበት ድምፀት፣ በሚያቀርባቸው አገላለጦች፣ በሚሰጣቸው ምሳሌዎች፣ በሚቀርብበት ተፋሰስ፣ በሚዋቀርበት አሰካክና በምጣኔው ይታወቃል፡፡ ሊደመጥ፣ ሊነበብ የሚችል፣ በሐሳቡ ባንስማማም በአቀራረቡ የሚማርከን፣ በዝርዝሩ ባንግባባም ሐሳቡ ግን የሚገባን፤ ባንወደውም የምናደንቀው ንግግር ከመሪዎች ይጠበቃል፡፡ ዐፄ ምኒልክ ለዐድዋ ጦርነት ሕዝቡን ለመጥራት ያወጁት ዐዋጅ ከዐዋጅነቱ ይልቅ የመሪ ጥሪ የሆነ ቃል አለው፡፡ በውስጡ ንጉሡንና ሕዝቡን የሚያቀራርብ፣ የሀገሪቱን ችግር የሚገልጥ፣ ከሕዝቡ የሚፈልጉትን የሚያሳይ፣ ሀገር ስትጠራው እምቢ ብሎ የቀረ የሚገጥመውን ዕጣ ፈንታ የሚያመላክት ቃል ነው፡፡ መላዋን ኢትዮጵያ ለአንድ ዓላማ ያሰለፈና ውጤቱን በዐድዋ ተራሮች ላይ ያሳየ ቃል ነው፡፡

በተለይ ደግሞ ሀገር ምጥ ላይ በምትሆንበት ጊዜ የመሪዎች ንግግር ወይ ፈዋሽ ወይ አባባሽ ይሆናል፡፡ ከአያያዝ ይቀደዳል ከአነጋገር ይፈረዳል እንዲሉ፡፡ አነጋገሩ የሚያግባባ፣ የሚጠራና የሚያቀራርብ ከሆነ ሕዝብን ለመፍትሔ የማሰለፍ ኃይል ይኖረዋል፡፡ ንግግሩ ብቻ ሳይሆን ንግግሩ የተዋቀረበት መዓዝን የመሪውን ጉዞ ካርታውን እንድናይ ያደርገናል፡፡

የዶክተር ዐቢይ አሕመድ ንግግር በንግግሩ ይዘት፣ ንግግሩ በተቀናበረባቸው ቃላት፣ ቃላቱ በተሰናሠሉበት አወቃቀር፣ ሐሳቡ በተገለጠባቸው ምሳሌዎች፣ ማሳያዎች፣ ጥቅሶች፤ ትኩረትና አጽንዖት በተሰጣቸው የሐሳብ ዘውጎች፣ ብርታቱና ድክመቱ ሊተነተንና የመሪዎች ንግግር ምን መሆን እንዳለበት መማማሪያ ሊሆን ይገባዋል የሚል ሐሳብ አለኝ፡፡ በዚህ ረገድ ንግግሩ የተዋቀረባቸውን ሰባት አዕማድ ለዛሬ ላንሳ፡፡
የዶክተር ዐቢይ የበዓለ ሲመት ንግግር በሰባት አዕማድ የተዋቀረ ነው፡፡ እነርሱም ክብር፣ ፍቅር፣ ተስፋ፣ አንድነት፣ ይቅርታ፣ ሰውነትና ኢትዮጵያ/ኢትዮጵያዊነት ናቸው፡፡

1.  ክብር፡- ዶክተር ዐቢይ ንግግራቸውን የጀመሩት ከእርሳቸው በፊት ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩትንና በፈቃዳቸው ሥልጣን ‹ያሸጋገሩትን› አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝን በማመስገን ነው፡፡ በዚህ ንግግራቸው ግን ክብርና ምስጋና የሰጡት ለእርሳቸው ብቻ አይደለም፡፡ ሌሎች ሰባት አካላትም ክብርና ምስጋና ተሰጥቷቸዋል፡፡

ሀ. ሽግግሩን እዚህ ደረጃ ለማድረስ ሚና ለተጫወቱ፣
ለ. ኢትዮጵያን ለሚያኮራት ታሪካችን፣
ሐ. ለኢትዮጵያውያን የማይበጠስ አንድነት፣
መ. ለኢትዮጵያ ታላቅነት በየዘመናቱ መሥዋዕትነት ለከፈሉ ጀግኖች አባቶቻችንና እናቶቻችን፣
ሠ. በውጭ ሀገር ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያን፣
ረ. ለተፎካካሪ ፓርቲዎች፣
ሰ. አሁን ለመጣው ለውጥ ዋጋ ለከፈሉ ኢትዮጵያውያን ተገቢውን ክብር በንግግራቸው ውስጥ  ሰጥተዋቸዋል፡፡ ሌላው ቀርቶ ከታሪክ መዝገብ የተፋቀ ይመስል ከመንግሥታዊ ዲስኩሮች ስሙ ጠፍቶ ለኖረው የካራማራ ድል ተገቢውን ክብር ሰጥተውታል፡፡

ኢትዮጵያውያንን የገለጡበት መንገድም ለዜጎች ያላቸውን ክብር የሚያሳይ ነበር ‹ኢትዮጵያ ማህጸነ ለምለም ናት። ከፍ ባለ የአገር ፍቅር መንፈስ ሰርክ የሚተጉልጆችን አፍርታለች። ልጆቿም ወደቀድሞ ክብሯ እንድትመለስ፣ የሕዝቧ ሰላምናፍትህ እንዲጠበቅ፣ ብልጽግና ያለ አድልኦ ለመላው ዜጎች ይደርስ ዘንድአጥብቀው ይመኛሉ… ይደክማሉ። በሀገር ውስጥና በውጪ ሆነው ስለ ሀገርአንድነትና ሰላም… ስለፍትህና እኩልነትእንዲሁም ስለብልጽግና ይጮሃሉይሞግታሉ… ይሟገታሉ።› ነው ያሏቸው፡፡ የዜጎቻቸውን ትግልና ጥረት ክብር ሰጥተውታል፡፡ አሸባሪዎች፣ ነውጠኞች፣ አደገኛ ቦዘኔዎች፣ አላሏቸውም፡፡ ዶክተር ዐቢይ ኢትዮጵያውያን ላደረጉት የዴሞክራሲ፤ የፍትሕ፤ የእኩል ተጠቃሚነት፤ በነጻ ተዘዋውሮ የመኖርና የመሥራት፤ የሕግ አስከባሪ ተቋማት ገለልተኝነት፤ ሕዝብ አገልጋዩን የመተቸት፤ የመምረጥ፣ የመጠየቅ ሙሉ መብትጥያቄና ትግል ክብርና ዕውቅና ሰጥተውታል፡፡ 
 
2. ፍቅር፡- አንድነታችን ፈተና ገጥሞታል፤ ፍቅራችንን የሚያቀዘቅዙ ነገሮች እየተከሠቱ ነው፣ መጠላላቱና መከፋፋቱ በየአቅጣጫው ዕየታየ ነው በምንልበት ወቅት ፍቅርን የሚሰብክ የመሪ መልእክት ኃይል አለው፡፡ የዶክትር ዐቢይ ንግግር ይህንን የተረዳና ማሻሪያ ለመስጠት የተዘጋጀ ነበር፡፡ በሕዝቡ መካከል ከፍቅር ይልቅ ቅሬታ፣ ከወዳጅነት ይልቅ ጠላትነት፣ የሚያጭሩ ቃላትን ላለመጠቀም ጥንቃቄ አድርጓል፡፡ በኢትዮጵያ ታሪክ ከደርግ ዘመን ፓርላማ ወዲህ ‹ፀር› ከፓርላማ የተባረረበት የመሪ ንግግር ነበር፡፡ ፀረ አብዮት፣ ፀረ ሕዝብ፣ ጸረ ልማት፣ ፀረ ዴሞክራሲ፣ ፀረ … የሚለውን እንደ ሃሌሉያ አዘውትሮ ሲሰማ ዐርባ ዓመት ላለፈው ፓርላማ እንግዳ ነገር ነው፡፡ ጠባብነት፣ ነፍጠኝነት፣ ኪራይ ሰብሳቢነት፣ ሽብርተኝነት፣ የመሳሰሉት የሰለቹ ቃላት ባመሳተፋቸው አዝነው የዋሉበት ንግግር ነበረ፡፡

የዶክተር ዐቢይ ንግግር በ8 ገጽ፣ በ2776 ቃላት፣ በ12533 ምዕራፍ አልባ ቅንጣቶች(Characters without space)፣ በ15230 ባለ ምዕራፍ ቅንጣቶች(Characters with space)፣ በ79 ዐንቀጾችና በ259 መሥመሮች የተዋቀረ ነው፡፡ በዚህ ንግግር ውስጥ በዋናነት የተንጸባረቀው መግለጫ ‹እኛ› የሚለው ራስን ከሕዝብ ጋር የሚያስተሣሥርና ፍቅርን ሊገልጥ የሚችለው አንጓ ነው፡፡ ይህን ለመግለጥ በቃላት ላይ - ችን የሚል ድኅረ ቅጥያ ተጠቅመዋል፡፡ ኢትዮጵያችን፣ ሕዝባችን፣ ሀገራችን፣ ወገናችን፣ ችግሮቻችን፣ ስኬቶቻችን የሚሉ መግለጫዎች አሉ፡፡ በጽሑፉ ውስጥ ይህንን መንገድ ከ86 ጊዜ በላይ ተጠቅመውበታል፡፡ ከዚህ መካከል ከ18 ጊዜ በላይ ‹ሀገራችን› የሚለው መግለጫ ይገኝበታል፡፡

3. አንድነት፡- የጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር፣ ከማራራቅ ይልቅ የሚያቀራርብ፣ ከመገፋፋት ይልቅ የሚያስተሣሥር፣ ከማግለል ይልቅ የሚያካትት፣ ከመነጣጠል ይልቅ የሚያስተባብር ነበር፡፡ ራሳቸውን የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር አድርገው ነው ያቀረቡት፡፡ ከመነሻቸው ይልቅ መድረሻቸው ላይ ነው ያተኮሩት፡፡ ራስ ካሣ እንዳሉት ‹ፀሐይን ለብቻዬ ልሙቅ አይባልም›፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩም የአንድ ወገን አይደሉም፡፡ የጥንቶቹም የዛሬዎቹም፣ የደጋፊዎቹም የተፎካካሪዎቹም፣ የክርስቲያኖቹም፣ የሙስሊሞቹም፣ የሌሎቹም፤ የመረጧቸውም ያልመረጧቸውም፣ የሀገር ቤት ነዋሪዎቹም የዳያስጶራዎቹም ጠቅላይ ሚኒስትር መሆናቸውን አሳይተውበታል፡፡ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር የትናንቱም የዛሬውም፣ የነገውም ጠቅላይ ሚኒስትር ነውና የቀደሙትን ከዛሬዎቹ ጋር አስተሣሥረው ጠርተዋቸዋል፡፡ በታሪካችን ውስጥ ማሳያ የሚሆኑትን ኩነቶች አንሥተው የእገሌ ጎሳ መሬት ነው ሳይሉ ኢትዮጵያውያን ለሀገራቸው በየዘመናቱ የከፈሉትን መሥዋዕትነትና በመሥዋዕትነት ቦታቸው የዚያው ቦታ አፈር ሆነው መቅረታቸውን ገልጠዋል፡፡ ‹በአንድ ሀገር ውስጥ የሀሳብ ልዩነቶች ይኖራሉ። የሀሳብ ልዩነት እርግማንአይደለም። ልዩነቱ እንዳለ ሆኖ መደማመጥና በመርሕ ላይ ተመስርተንመግባባት ስንችል የሀሳብ ልዩነት በረከት ይዞልን ይመጣል። በሀሳብ ፍጭትውስጥ መፍትሄ ይገኛል። በመተባበር ውስጥ ኃይል አለ። ስንደመርእንጠነክራለን። አንድነት የማይፈታው ችግር አይኖርም… አገር ይገነባል። የኔሀሳብ ካላሸነፈ ሞቼ እገኛለሁ ማለት ግን እንኳን አገርን ሊያቆም ቤተሰብንያፈርሳል። ያለችን ኢትዮጵያ ነች ከየትኛውም የፖለቲካ አመለካከት በላይ ሀገራዊአንድነት ይበልጣል። አንድነት ማለት ግን አንድ ዓይነትነት ማለት እንዳልሆነሊሰመርበት ይገባል። አንድነታችን ልዩነቶቻችንን ያቀፈ ብዝኃነታችንን በኅብረብሔራዊነት ያደመቀ መሆን አለበት።› የሚለው መዓዝናዊ የአንድነት መግለጫቸው ነው፡፡

ይህ ለውጥ እንዲመጣ በየመሥመራቸው የታገሉትን የጠሩበት መንገድ፣ ተቃዋሚ ፓርቲ እየተባሉ ሲጠሩ የኖሩትን ኃይሎች ‹ተፎካካሪ ፓርቲዎች› ብለው የገለጡበት አካሄድ፡፡ ዳያስጶራውን ማኅበረሰብ ያቀረቡበት መንገድ የንግግሩ አንኳር ነው፡፡ ከዚህ በፊት ከተለመደው ወጣ ባለ መልኩ በተለያየ ጊዜ፣መስዋእትነት ለከፈሉ የመብት ተከራካሪዎችና ፖለቲከኞች፤ በቅጡ ሳይቦርቁሕይወታቸውን ለተቀጠፈ ለውጥ ፈላጊ ወጣቶች፤ ለሥነ ልቦናዊና አካላዊ ቀውስየተዳረጉ ቤተሰቦችና ግለሰቦች› እና ‹ሰላም ለማስከበርና ሕገመንግሥታዊ ግዴታቸውን ለመወጣት ሲንቀሳቀሱ ሕይወታቸውን  የፀጥታ ኃይሎች› ጎን ለጎን የተመሰገኑበት መንገድ አስደናቂ ነው፡፡ መንግሥት ለአንጋቹ እንጂ ለሟቹ የማይወግንበትን አካሄድ ያረመም ነው፡፡

4. ይቅርታ፡- የጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር ከተዋቀረባቸው አዕማድ አንዱ ይቅርታ ነው፡፡ በተለያዩ መንገዶች ገልጠውታል፡፡ በተለይም ስድስቱ ዋና ዋና ዘውጎች ይጠቀሳሉ፡-

፩. ያሳካናቸው በርካታ ድሎች እንዳሉ ሁሉ በፍጥነት መቀረፍ የሚገባቸውበርካታ ጉድለቶች እንዳሉም እናምናለን። ከስህተቶቻችን ተምረን ወደፊትበመራመድ ማተኮር ያለብን ጉዳይ የተሻለች ሀገር ለሁላችንም በመገንባቱ ላይነው።›፣‹የሁሉም ዜጎችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት፣ ማኅበራዊ ፍትሕ እናፖለቲካዊ ተሳትፎ ከማሳደግ አንጻር ክፍተቶች ነበሩ።› የሚለው ስሕተትን የሚያምነው፤

. ‹ወቅቱ ከስህተታችን ተምረን አገራችንን የምንክስበት ወቅት ነው!› የሚለው ወቅቱን ከስሕተት አንጻር የገመገመው፡፡

፫.  ‹በተለያየ ጊዜ፣ መስዋእትነት ለከፈሉ የመብት ተከራካሪዎችና ፖለቲከኛች፤በቅጡ ሳይቦርቁ ሕይወታቸውን ለተቀጠፈ ለውጥ ፈላጊ ወጣቶች፤ ለሥነ ልቦናዊና አካላዊ ቀውስ ለተዳረጉ ቤተሰቦችና ግለሰቦች ከልብ የመነጨ ይቅርታእጠይቃለሁ› የሚለው ለተፈጠረው ችግር ይፋዊ ይቅርታ የሚጠይቀው፣

.‹በአገር ውስጥም ሆነ በስደት ከአገር ውጭ የምትኖሩ ኢትዮጵያውያንናትውልደ ኢትዮጵያውያን በሙሉ ከልባችን ይቅር ተባብለን፣ የትናንትናውንምእራፍ ዘግተን፣ በብሔራዊ መግባባት ወደ ቀጣይ ብሩህ ሀገራዊ ምእራፍእንሻገር ዘንድ ጥሪዬን አቀርባለሁ› የሚለውና ከሌላውም ወገን ይቅርታን የሚጠይቀው ንግግር ይቅርታውን በየደረጃው የጠየቀ ነው፡፡

.  ‹መጪው ጊዜ በኢትዮጵያችን የፍቅርና የይቅርታ ጊዜ ነው!› ሲሉም ይሄንኑ አጽንተውታል፡፡ ይህም እንዲሳካ

፮.‹በአገር ውስጥም ሆነ በስደት ከአገር ውጭ የምትኖሩ ኢትዮጵያውያንናትውልደ ኢትዮጵያውያን በሙሉ ከልባችን ይቅር ተባብለን፣ የትናንትናውንምእራፍ ዘግተን፣ በብሔራዊ መግባባት ወደ ቀጣይ ብሩህ ሀገራዊ ምእራፍእንሻገር ዘንድ ጥሪዬን አቀርባለሁ፡፡› ሲሉም ጥሪ አቅርበዋል፡፡ 

5. ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት፡- ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ ምን ዓይነት ናት? እነዚህን 12 መግለጫዎቻቸውን እንመልከት፡-

 ሀ. ኢትዮጵያ ማኅጸነ ለምለም ናት
ለ. ትላንት፣ አባቶቻችን በመተማ፣ በማይጨውና በካራ ማራአጥንታቸውን ከስክሰው የከበረ ደማቸውን አፍስሰው በክብርናበአንድነት ያቆይዋት አገር አለችን።
ሐ. እኛ ዕድለኞች ነን። ውብ አገር አኩሪ ታሪክ አለን። እኛ መነሻችንንእናውቃለን። በርካታ ዘመናትን የሚሻገር ታሪክ ያለው ታላቅ ዝብ ነን።
.ኅብረታችን ለዓለም ምሳሌ መሆን ይችላል። ጠላቶቻችንንአንበርክኳል። ሉዓላዊነታችንን ጠብቆ ዛሬ ላይ ከማድረሱም በላይለሌሎች ሕዝቦችም የነጻነት ትግል አርአያ ሆኗል።
ሠ. ማንነታችንን እንዳይለያይ ሆኖ የተሰናሰለ፣ እንዳይነጣጠል ሆኖየተገመደ፣የተዋደደ እና የተዋሐደ ነው!
.የየትኛውንም ኢትዮጵያዊ ክቡር ሥጋና ደም በየትኛውም የኢትዮጵያክፍል ውስጥ አፈር ሆኖ ታገኙታላችሁ። ኢትዮጵያውያን ስንኖርኢትዮጵያ ስንሞት ደግሞ ኢትዮጵያ እንሆናለን።
. ኢትዮጵያ የሁላችን ሀገር፤ የሁላችን ቤት ናት!
ሸ. ያለችን ኢትዮጵያ ነች ከየትኛውም የፖለቲካ አመለካከት በላይ ሀገራዊ አንድነትይበልጣል።
ቀ. እኛ ኢትዮጵያውያን ዲሞክራሲና ነጻነት ያስፈልገናል፣ ይገባናልም !በ. ኢትዮጵያ የጋራችን፣ የኛ የሁላችን መሆኗን ተገንዝበን የሁሉምድምጽ የሚሰማበት፣ ሁላችንንም የሚያሳትፍ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓትየመገንባቱን ትግል አጠናክረን እንቀጥላለን።
. ኢትዮጵያችን፣ አንዱ ሠርቶ ሌላው ቀምቶ የሚኖርባት አገር እንዳትሆን  ቸ. እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ለሥራም ሆነ ለትምህርት በሄደበት ሁሉ ኢትዮጵያንተሸክሟት ይዞራል። ኢትዮጵያዊውን ከኢትዮጵያ ታወጡት እንደሆነ ነው እንጂ ኢትዮጵያንከኢትዮጵያዊው ልብ ውስጥ አታወጧትም የሚባልም ለዚህ ነው። 

የጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር ኢትዮጵያዊነትን ከዜግነት በላይ ሐሳብ፣ ፍልስፍናና ሀገራዊ መርሕ አድርጎ ያቀረበ ነው፡፡
ይህንንም በአንድ አንኳር ‹ኢትዮጵያዊነት ያስተማረን እውነታበጊዜያዊ ችግሮች ተሸንፎ መውደቅን ሳይሆን ፈተናዎችን ወደ ዕድልና መልካምአጋጣሚቀይሮ ድል መቀዳጀትን ነው።› ኢትዮጵያን ብቻ ሳይሆን ‹ኢትዮጵያዊነት› የሚለውን ሉዓላዊ ሐሳብ በክብር ገልጠውታል፡፡

 6. ሰውነት፡- ማንኛውም መሪ፣ መሪ ከመሆኑ በፊት ሰው ነው፡፡ አብዮታዊ ነን የሚሉ መሪዎች ሰውነትን ይተውትና ተቋማዊነትን ቦታ ይሰጡታል፡፤ ከሰው የተወለዱ፣ ሰው ያሳደጋቸውና የሰው ፍሬዎች መሆናቸው ይረሱታል፡፡ መነሻቸውን ከሰው ሳይሆን ከድርጅት ያደርጉታል፡፡ የዶክተር ዐቢይ ንግግር አንዱ ዓምድ ለሰውነት የሰጠው ቦታ ነው፡፡ ሴቶች፣ ወጣቶች፣ ዳያስጶራዎች፣ መሥዋዕትነት የከፈሉ ዜጎች የተነሡበት መንገድ ለሰውነታቸው ቅርብ በሆኑ ቃላት ነው፡፡ እንደ ቡድን የሚያይ ሳይሆን ለግለሰብነታቸው ዋጋ የሚሰጥ ነው፡፡ ዳያስጶራዎች በምንም ዓይነት የፖለቲካ መሥመር ውስጥ ቢሆኑም ‹ሁላችሁምበታታሪነታችሁ፣ በልቀታችሁ እና የትም በሚከተላችሁ የሀገራችሁ የጨዋነትባሕሪ የኢትዮጵያና የዕሴቶቿ እንደ ራሴዎች ናችሁ።› የሚለው ገለጻ ግን የማይመለከተው የለም፡፡ ‹አንዳንድ ጊዜ ከኢትዮጵያ ያነሰ የተፈጥሮም ሆነ የታሪክሀብት ባላቸው ነገር ግን እጅግ በበለጸጉ ሀገራት ውስጥ ራሳችሁን ስታገኙትስለሀገራችሁ ቁጭት ሳይሰማችሁ አይቀርም።› ሲል ቁጭታቸውን ይቆጫል፡፡ ተፎካካሪ ፓርቲዎችን ‹እንደጠላት ሳይሆን እንደ ወንድም፣ አማራጭ ሀሳብ አለኝብሎ እንደመጣ አገሩን እንደሚወድ የዜጋ ስብስብ› ለማየት ጥረዋል፡፡ ከድርጅቶቹ ይልቅ ሰዎቹን ‹ወንድም፣ ዜጋ› እያሉ በሰውነት ጠርተዋቸዋል፡፡ ከዚህ በፊት ባልተለመደ መልኩም እናታቸውን፣ ባለቤታቸውንና የትግል አጋሮቻቸውን ያመሰገኑበት መንገድ ሰውዬው ሰው ናቸው እንድንል የሚያደርግ ነው፡፡ እናታቸውን ከኢትዮጵያውያን እናቶች አንዷ አድርገው፣ ባለቤታቸውን ሚና ከኢትዮጵያውያን ሚስቶች ጋር አስተሣሥረው የገለጡበት መንገድ ‹ሰውነት› የታየበት ነው፡፡ ሰው ከሆኑ ደግሞ እንደሰው ይሠራሉ፣ እንደሰውም ይሳሳታሉ፡፡

7. ተስፋ፡- ሰባተኛው የንግግሩ ዓምድ ተስፋ ነው፡፡ ምን ሊሠሩ አስበዋል? ምን እንጠብቅ? ሊሠሩ ያሰቡትን ብቻ ሳይሆን ከሌሎች አካላት የሚፈልጉትንም ገልጠውበታል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር ውስጥ ቃል መግባትንና ጥሪን የተመለከቱ 19 ጉዳዮች አሉ፡፡ እነዚህም፡-
       i.   ይህ የሥልጣን ሽግግር አዲስ ምዕራፍ የምንጀምርበት ሌላ ታሪካዊ እድልነው፤ በመሆኑም በከፍተኛ የኃላፊነት  ስሜት ልንጠቀምበት ይገባል።

ii.  በሀገራችን ዲሞክራሲ እንዲያብብ፣ ነጻነትና ፍትሕ እንዲሰፍን፣ የሕግየበላይነት እውን እንዲሆን አስፈላጊውን 
ማሻሻያ በማድረግ በዘርፉያለውን ክፍተት እንሞላለን።

iii.  ከኤርትራ መንግሥት ጋር ለዓመታት ሰፍኖ የቆየው አለመግባባትእንዲያበቃም ከልብ እንፈልጋለን። 
የበኩላችንንም እንወጣለን።

iv.  ኢትዮጵያችን፣ አንዱ ሠርቶ ሌላው ቀምቶ የሚኖርባት አገር እንዳትሆንለመጠበቅ የምንችለውን ሁሉ 
እንድናደርግ በትህትና እጠይቃችኋለሁ

v.   አሁን በጀመርነው አዲስ ምዕራፍ፣ ዘረፋን፣ የሀብት ብክነትን እናየተደራጀ ሙስናን፣ መላው ሕዝባችንን 
በሚያሳትፍ እርምጃ ለመመከትሌት ተቀን እንተጋለን።

vi.   በተለይም ከከፍተኛ ትምህርት ተቋሞቻችን እና ከቴክኒክ እና ሙያኮሌጆች የሚወጡት ተማሪዎቻችን 
ከሚገበዩት ዕውቀት የሚነጻጸርከሂሎት እንዲኖራቸው ከፍተኛ ጥራት ይደረጋል።

vii.  የሁለተኛውን የዕድገት እና ትራንስፎርሜሽን እቅድ የሁሉት ዓመት ተኩልአፈጻጸም በመገምገም አስፈላጊ 
የሆኑ የፖሊሲ እርምጃዎችን በመውሰድ፣ፈጣን የኢኮኖሚ እድገትን ለማስቀጠል እንታገለን

viii.  ኢትዮጵያ ለወጣቶቿ ተስፋ የምትሰጥ እንጂ፣ ተስፋ የምታስቆርጥ አገርእንዳትሆን የምንችለውን ሁሉ 
እንደምናደርግ ቃል እገባለሁ።በሚቀጥሉት ጊዜያት ለወጣቱ የሥራ ዕድል መፍጠር ብቻ ሳይሆንወጣት 
ባለሀብቶች በብዛት እንዲፈጠሩ እንሠራለን። ለዚህ እንቅፋትናመሰናክል ለሚሆኑ አመላካከቶችና የተንዛዙ 
አድሏዊ የሆኑ አሠራሮችተወግደው ፍትኃዊ የማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ሥርዓት እንዲኖረንመንግሥት ምቹ ሁኔ
ይፈጥራል።

ix.   መንግሥታችን ከዚህ ቀደም ከነበረው ፍጥነት እና የትግበራ ስኬት በላቀመልኩ ለሴቶች ሁሉን አቀፍ ተሳትፎ እና ተጠቃሚነት በቁርጠኝነትይሠራል።

x.   ዜጎች በሀገራቸው ውስጥ ከቦታ ቦታ የመዘዋወር እና ሀብት የማፍራትመብታቸው መከበር አለበት። 
በመሆኑም እንደዚህ ዓይነት ተገቢ ያልሆነድርጊት እንዲያበቃና ዳግም እንዳይፈጠር መሥራት ይኖርብናል።

xi. በቀሪው የሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ዓመታት ቀሪየልማት መርሐ ግብሮቻችንን በፈጠነ ጊዜ ለማሳካት ጥረት ይደረጋል።

xii.   ከመደበኛው የሥራ ሰዓታችን በሚሻገር ጊዜ፣ ከፍ ባለ ፍጥነትና ተነሳሽነትበመሥራት በቅርብ ዓመታት 
ውስጥ በተከሰተው ፖለቲካዊ አለመረጋጋትየደረሰብንን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ጉዳት ለማካካስ አገራዊ ንቅናቄ
እንድናደርግ ከአደራ ጭምር መልዕክቴን አስተላልፋለሁ።

xiii.   ዕውቀታችሁንና ልምዳችሁን ይዛችሁ ወደ ሀገራችሁ መመለስናሀገራችሁን አልምታችሁ መልማት ለምትሹ ሁሉ እጃችንን ዘርግተንእንቀበላችኋለን።

xiv.   በውጭ ሀገራት ኑሯችሁን ላደረጋችሁትም ቢሆን በማንኛውም መልኩበሀገራችሁ ጉዳይ ላይ ንቁ ተሳታፊ
 እንድትሆኑና ሀገራችንን በሙሉምመልክ ለመቀየር ለምታደርጉት አስተዋጽኦ መንግሥት ያልተቆጠበ ድጋፍ 
ማድረጉን ይቀጥላል።

xv.   ከጎናችን የቆማችሁ የልማት አጋሮቻችን የሀገራችን ጥብቅ ወዳጆችእንደሆናችሁ እንገነዘባለን። የሀገራችንን ልማት እና ሰላም ለማረጋገጥበምናደርገው ጥረት እንደ ወትሮ ሁሉ ከጎናችን እንደምትቆሙ ባለሙሉ ተስፋ ነኝ።

xvi.   ለተፈጠሩ ችግሮች እልባት በማበጀት ሕዝባችንን እንደምንክስም ጭምርበዚሁ አጋጣሚ ቃል እገባለሁ፡፡

xvii.   በልዩ ልዩ መንገድ የምትታገለግሉ የተፎካካሪ ፓርቲ መሪዎች፣አብሮነታችንንና ሰላማችንን አደጋ ላይ
 የሚጥሉ፤ ብሔራዊጥቅሞቻችንንም አሳልፈው የሚሰጡ የአስተሳሰብ መስመሮችን በአርቆአስተዋይነትና ሀገራዊ 
ፍቅር፤ በሰጥቶ መቀበል መርሕ የተሻለ የፖለቲካባህል ለመፍጠር የምናደርገው ጥረት እንድታግዙ ጥሪዬን
አስተላልፋለሁ፡፡

xviii.   ሁላችንም የዳበረ ዴሞክራሲ ለመገንባት እንረባረብሀገራችንን ከድህነትአዘቅት ውስጥ ለማውጣት እንትጋዘረኝነትና መከፋፈልን ከሀገራችንእናጥፋየተማረና በምክንያት የሚከራከር ዜጋ እንፍጠር!

xix.   ከግድቡ መጠናቀቅ ባሻገር የሀገራችንን ብልጽግና እስከምናረጋግጥበትከፍታ ድረስ እንድንዘልቅ ጥሪዬን 
አቀርባለሁ፡፡

ከእነዚህ መካከል 11ዱ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ወይም መንግሥትን የሚመለከቱ ሲሆኑ 8ቱ ደግሞ ጥሪ  ተደረገላቸውን አካላት የሚመለከቱ ናቸው፡፡ ይህም የችግሩ ዋና መነሻ የመንግሥት አካሄድ ነውና የመፍትሔው ዋና ቁልፍም በመንግሥት እጅ መሆኑን ያሳያል፡፡

 የጠቅላይ ሚኒስትሩ ቃልና ጥሪ 19 ርእሰ ጉዳዮችን የተመለከተ ነው፡፡

፩. የሥልጣን ሽግግሩን አጠቃቀም
፪. የዴሞክራሲ ጥያቄ
፫. የፍትሕ ጥያቄ
፬. የኤርትራን መንግሥት የተመለከተ
፭. ፍትሐዊ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት
፮. ሙስና
፯. የትምህርት ጥራት
፰. የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅዱ
፱. የኢኮኖሚ ፖሊሲው ማሻሻያ
፲. ለወጣቱ ምቹ የምትሆን ሀገር
፲፩. የሴቶች ተጠቃሚነት
፲፪. ከቦታ ቦታ የመዘዋወርና የመሥራት መብት
፲፫. በተፈጠረው የፖለቲካና የኢኮኖሚ ኪሣራ የተቸገረውን ሕዝብ መካስ
፲፬. የተፈጠረውን የፖለቲካና የኢኮኖሚ ኪሣራ የሚያካክስ ሥራ መሥራት
፲፭. ዳያስጶራ
፲፮. የልማት አጋሮች
፲፯. ተፎካካሪ ፓርቲዎች
፲፰. ዘረኝነትና መከፋፈል
፲፱. የሕዳሴው ግድብ ናቸው፡፡

እነዚህን ነገሮች ተግባራዊ አድርጎ የሚፈለገውን ለውጥ ለማምጣት ቁርጠኝነት፣ ቁርጥ ያለ ዕቅድ፣ አካታች የሆነ አካሄድ፣ ሳይዘናጉ መፍጠንና ከአንኳር የሕዝብ አካላት ጋር መወያየትን ይጠይቃል፡፡ በተመሳሳይ መንገድ ተጉዞ የተለየ ውጤት ማምጣት አይቻልም፡፡ ‹ቃል ይቀድሞ ለነገር› ነውና ይህ ቃል የነገው ተግባር መግቢያ ነው ብለን እናምናለን፡፡ በኢትዮጵያ የቅርብ ዘመን ታሪክ እንደታየው ሕዝብ ዕድል ይሰጣል፡፡ ሕዝቡ የሰጠውን ዕድል የማይጠቀሙ መሪዎች ሲገጥሙት ግን በአሳቻ ሰዓት እንደተመካከረ ሰው ‹ሆ› ብሎ ይነሣል፡፡ ዝምታውን እንደ መሸነፍና ፍርሃት የሚቆጥሩ መሪዎች ዋጋ ከፍለውበታል፡፡ የሀገራችን ሊቃውንት ሁለት ዓይነት መብራት አለ ይላሉ፡፡ አንዱ ፏ ብሎ የሚበራና መንገዱን ወገግ አድርጎ የሚያሳይ ነው፡፡ ሌላኛው ደግሞ ከሩቁ ሆኖ መድረሻን የሚጠቁም መብራት ነው፡፡ የመጀመሪያው ከተገኘ መንገዱን ያለ ዕንቅፋት ለመሄድ፣ በቶሎም ለመድረስ ይመቻል፡፡ እርሱ ካልተገኘ ደግሞ ማዶ ተሰቅሎ መድረሻውን የሚጠቁመው መብራት መኖር አለበት፡፡ መንገዱን ወገግ አድርጎ ባያሳይም መድረሻውን ያመለክታል፡፡ የሚጓዘው ሰው እየወደቀም እየተነሣም ይሄዳል፤ መድረሻውን ያውቀዋልና፡፡ በሩቁ ስለሚያየው አይስተውም፡፡ ተስፋ አይቆርጥም፣ እንደሚደርስ ርግጠኛ ነውና፡፡ ድቅድቅ ጨለማ ግን እንኳን ለሀገር ለግለሰብም አስቸጋሪ ነው፡፡ የዶክተር ዐቢይ መንግሥት ይህ የሕዝብ ድጋፍና ፍቅር እንደ በረዶ ከመቀዝቀዙ በፊት ቢችል መንገዱን ያብራ፣ ባይችል መድረሻውን ያሳይ፡፡ ካልሆነ ግን ምናልባት ሌሎቹ ቀደምቶቹ ያገኙትን ዕድል ላያገኘው ይችል ይሆናል፡፡ ሰው የሚጠየቀው በተሰጠው መጠን ነውና፡፡ አሁን ተግባሩን እንጠብቃለን፡፡ ችግሮቹን ሁሉ እንዲፈቱ ሳይሆን መፍታት እንዲጀምሩ፤ ስሕተቶቹን ሁሉ እንዲያርሙ ሳይሆን ማረም እንዲጀምሩ፤ መንገዱን በሙሉ እንዲሠሩ ሳይሆን መሥራት እንዲጀምሩ፡፡

ወቅቱ የትንሣኤ ዋዜማ ነውና እባክዎን ሥራዎትን መፈታት የሚገባቸውን የፖለቲካ እሥረኞች (በተለይም ደግሞ ይህንን የእርስዎን ንግግር ከእሥር ቤት ውጭ እንዲሰሙ ከተፈቱ በኋላ፣ እሥር ቤት ተመልሰው የሰሙትን እነ እስክንድር ነጋን) ና መነኮሳቱን በመፍታት ይጀምሩ፡፡ የእርስዎም የሕዝቡም ፋሲካ ደርብ ፋሲካ እንዲሆን፡፡ 
ይቅናዎት፡፡