Friday 30 May 2014

ካርልኃይንስ በኧም አረፉ

በወጣትና በጎልማሳነታቸዉ ዘመን በተጫዎቷቸዉ ፊልሞች ኦስትሪያና ጀርመን ዉስጥ ከፍተኛ አድናቆትና ያተረፉት በኧም ኢትዮጵያ ዉስጥ ችግረኞችን የሚረዳዉን ሜንሽን ፉር ሜንሽን የተሠኘዉን ግብረ-ሠናይ ድርጅት የመሠረቱና ለረጅም ጊዜ የመሩ በጎ አድራጊም ነበሩ


ኦስትሪያዊዉ የፊልም ተዋኝና በጎ የአድራጊ ድርጅት መሥራች ካርልሐይንስ በኧም አረፉ። 86 ዓመታቸዉ ነበር።በወጣትና በጎልማሳነታቸዉ ዘመን በተጫዎቷቸዉ ፊልሞች ኦስትሪያና ጀርመን ዉስጥ ከፍተኛ አድናቆትና ያተረፉት በኧም ኢትዮጵያ ዉስጥ ችግረኞችን የሚረዳዉን ሜንሽን ፉር ሜንሽን የተሠኘዉን ግብረ-ሠናይ ድርጅት የመሠረቱና ለረጅም ጊዜ የመሩ በጎ አድራጊም ነበሩ። በኧም የመሠረቱትና የመሩት ድርጅት ኢትዮጵያ ዉስጥ ሰወስት ሆስፒታሎችን ጨምሮ አንድ መቶ የጤና ተቋማትን፤ ከሰወስት መቶ ስልሳ በላይ ትምሕርት ቤቶችን አስገንብቷል። ታዋቂዉ የቀድሞ ፊልም ተዋናይና «ሰዎች ለሰዎች» የተሰኘዉ የርዳታ ድርጅት መሥራች የ86 ዓመቱ ካርል ኃይንስ በኧም ትናንት ምሽት በኦስትርያ ዛልስቡርግ ከተማ አጠገብ በምትገኘዉ ጎርዲግ ከተማ ዉስጥ ማረፋቸዉን የከተማዉ ቃል አቀባይ ገልጿል። «ሜንሽን ፎር ሜንሽን» የተሰኘዉ ግብረሰናይ ድርጅት መሥራች ካርል ኃይንስ በኧም በጎርጎረሳዉያኑ 1950 ዓ,ም ሲሲ በተሰኘዉ ፊልም ላይ ንጉስ ፍራንዝ ዮሴፍ በሚል፤ ገጸ-ባህሪ እጅግ ከፍተኛ እዉቅናን ማግኘታቸዉ ይታወቃል። ትዉልዳቸዉ በጀርመን ዳርምሽታት ከተማ የሆነዉ ካርል ኃይንዝ በኧም፤ ለረጅም ግዜ ታመዉ የአልጋ ቁራኛ እንደነበሩም ተመልክቶአል። በዚህም ኢትዮጵያዉያንን ለመርዳት ያቋቋሙት «ሰዎች ለሰዎች» የተሰኘዉን ድርጅት ኢትዮጵያዊት ባለቤታቸዉ ወ/ሮ አልማዝ በኧም ለጥቂት ዓመታት በዋና ተጠሪነት ሲያስተዳድሩ ከቆዩ በኃላ፤ ከባለፈዉ ዓመት ታሕሳስ ወር ጀምሮ ባለቤታቸዉን ካርል ኃይንዝ በኧምን ለማስታመም፤ ድርጅቱን በዋና ኃላፊነት መምራት ማቆማቸዉ ይታወቃል። ድርጅታቸዉ በመሥራቹ ሞት የተሠማዉን ሐዘን ገልጿል። 


No comments:

Post a Comment