Thursday 5 July 2018

የሃይማኖት አባቶች ተጣልተው ፖለቲከኞች ታረቁ እያሏቸው ነው

ምላጩ አብጦ ውኃው አንቆ

‹ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡታል፣ ውኃ ቢያንቅ በምን ይውጡታል› ይላል የሀገሬ ሰው፡፡ የኢትዮጵያም አንዱ ችግሯ ይኼ ነው፡፡ የምላጭ ማበጥና የውኃ ማነቅ፡፡ የተጣሉትን አስታራቂ፣ የተለያዩትን አንድ አድራጊ መሆን የነበረባቸው የሃይማኖት አባቶች ተጣልተው ፖለቲከኞች ታረቁ እያሏቸው ነው፡፡ ለፍትሕ ዘብ ቆመው፣ ደኻ አንዳይበደል ፍርድ እንዳይጓደል ማድረግ የነበረባቸው የዳኝነት አካላት ዜጎች እንዲበደሉ፣ የፍርድ ሚዛን እንዲያዘነብል፣ ግፈኞች በሕግ ስም የፈለጉትን እንዲያደርጉ መሣሪያ ሆነዋል፡፡ ዜጎችን በሕግ ጥላ ሥር ለማረም የተዘጋጁ ማረሚያ ቤቶች የሰዎች ‹ቄራ› ሆነዋል፡፡ የዜጎችን ችግር ለመፍታት የተቋቋሙ የ‹ኢሚግሬሽን› ቢሮዎች የዜጎች ማኘኪያ› ሆነዋል፡፡ 

ከጥንት ዘመን ጀምሮ ከአውሮፓና ከእስያ የመጡ ስደተኞችን እየተቀበለ ከዜጋውም በላይ ክብርና ፍቅር ሲሰጥ የኖረ ማኅበረሰብ የገዛ ወገኑን ‹ውጣልኝ፣ ሂድልኝ፣ አልይህ፣ አልስማህ› ይላል፡፡ ከሺ ዓመታት በላይ የነጻነት ታሪክ የሚቆጥር ሕዝብ አሁንም ‹ነጻ አውጭ ድርጅት› ይመሠርታል፡፡ የእርሱን ሰንደቅ ዓላማ የነጻነት ዓርማ አድርጎ ለጥቁር ሕዝብ የሰጠ ሕዝብ እንደገና በሰንደቅ ዓላማ ላይ ይከራከራል፡፡ አፍሪካ ተከፋፍላ መነጋገርና መገናኘት ባቃታት ጊዜ ምዕራብና ምሥራቅ ዞሮ የአፍሪካን አንድነት ያመጣ ሕዝብ እርሱ ራሱ ተከፋፍሎ መከራውን ያያል፡፡ እነ እገሌ ‹እኛ ታግለን ባመጣነው ለውጥ እኛው መጠቀም አለብን› አሉ እያለ ሲያማርር የኖረ ወገን እርሱ ታግሎ ሌላ ለውጥ ያመጣ ሲመስለው፣ እርሱም በተራው ‹እኛ ታግለን ባመጣነው ለውጥ ሌላ ተጠቀመበት› እያለ ያላዝናል፡፡ አስገራሚ ነው መቼም፡፡
ውኃ አንቆ ምላጭ አብጦ መከራችን እናያለን፡፡

Daniel Kibert

No comments:

Post a Comment