Sunday 16 June 2013

መምህራን በሕፃናት ላይ ግብረሰዶም በመፈጸም ወንጀል ተጠርጥረው ተከሰሱ


የዋስትና መብታቸው ተገፎ ማረሚያ ቤት እንዲቆዩ ተደርገዋል
-አካዳሚውም ተገቢ ጥበቃ ባለማድረጉ በክሱ ተካቷል
በቦሌ ክፍለ ከተማ ልዩ ቦታው ሩዋንዳ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ በሚገኘው ካራክተር ሆልማርክ አካዳሚ በሚባል ትምህርት ቤት ግቢ ውስጥ፣ በሁለት ወንድ ሕፃናት ላይ ግብረሰዶም ፈጽመዋል የተባሉ ስድስት መምህራን ተጠርጥረው ክስ ተመሠረተባቸው፡፡
 ተጠርጣሪዎቹ የአካዳሚው ዳይሬክተር አቶ ደሳለኝ ኃይለየሱስ፣ የአካዳሚው ሱፐርቫይዘር አቶ የኔዓለም ጌታቸው፣ መምህር ዓለማየሁ ገብሬ፣ መምህር ደበበ ጥሩነህ፣ አቶ መልካሙ ቀለብና አቶ ሳምሶን መኩሪያ ሲሆኑ፣ አካዳሚው ካራክተር ሆልማርክ አካዳሚ አክሲዮን ማኅበርም መከሰሱን የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ ለፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ለሰባተኛ ወንጀል ችሎት ያቀረበው ክስ ያስረዳል፡፡ 
ተጠርጣሪዎቹ የ10 እና የ11 ዓመት ዕድሜ ያላቸውን ሁለት ወንድ ሕፃናትን ከጥቅምት ወር መጀመሪያ 2005 ዓ.ም. ጀምሮ በምሳና በዕረፍት ጊዜ ተማሪዎች ከክፍል ሲወጡ፣ ወደ ባዶ ክፍል በመውሰድ በተደጋጋሚ እየተፈራረቁ የግብረሰዶም ድርጊት እንደፈጸሙባቸው ክሱ ያስረዳል፡፡ በተለያዩ ጊዜያት ዳይሬክተሩንና ሱፐርቫይዘሩን ጨምሮ ሌሎቹም መምህራንም በየካቲት ወር ሁለት ቀናት፣ እንዲሁም በሚያዝያ ወር በሕፃናቱ ላይ ድርጊቱን ፈጽመዋል በሚል ተጠርጥረው፣ የሕፃናት ክብር ድፍረት ወንጀል ተካፋይ በመሆን መከሰሳቸውን ክሱ ያብራራል፡፡ 
ካራክተር ሆልማርክ አካዳሚ አክሲዮን ማኅበር በሥሩ ያሉትን ሠራተኞችና ኃላፊዎች በአግባቡ መቆጣጠርና የሕፃናትን ጤንነትና አካልን በአግባቡ መጠበቅ ሲገባው ባለመፈጸሙ፣ በወንጀል ድርጊቱ ተካፋይነት ተጠርጥሮ መከሰሱን ክሱ ይገልጻል፡፡
ተጠርጣሪዎቹ ፍርድ ቤት ቀርበው ድርጊቱን አለመፈጸማቸውን በመግለጽ የዋስትና መብታቸው እንዲጠበቅላቸው ቢጠይቁም፣ ድርጊቱ ከባድ መሆኑን በመግለጽ ፍርድ ቤቱ የዋስትና መብታቸውን ውድቅ በማድረግ፣ የዓቃቤ ሕግ ምስክሮችን ለመስማት ለሰኔ 14 ቀን 2005 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ ተጠርጣሪዎቹም በማረሚያ ቤት እንዲቆዩ አዟል፡፡

http://www.ethiopianreporter.com/index.php/news/item/2189-%E1%88%98%E1%88%9D%E1%88%85%E1%88%AB%E1%8A%95-%E1%89%A0%E1%88%95%E1%8D%83%E1%8A%93%E1%89%B5-%E1%88%8B%E1%8B%AD-%E1%8C%8D%E1%89%A5%E1%88%A8%E1%88%B0%E1%8B%B6%E1%88%9D-%E1%89%A0%E1%88%98%E1%8D%88%E1%8C%B8%E1%88%9D-%E1%8B%88%E1%8A%95%E1%8C%80%E1%88%8D-%E1%89%B0%E1%8C%A0%E1%88%AD%E1%8C%A5%E1%88%A8%E1%8B%8D-%E1%89%B0%E1%8A%A8%E1%88%B0%E1%88%B1

No comments:

Post a Comment