Sunday 23 December 2012

በኩዌት በሳዑዲ ዓረቢያና ጅዳ የኢትዮጵያ ኤምባሲ የሰው ኃይልን በርካሽ ዋጋ ሊያቀርብ እንደሚችል በአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ማስታወቂያው እያስነገረ ነው፡፡

Hellen Zewdu
 
ሰው በፈለገበት ቦታና አገር የመዘዋወር መብቱ በሕገ መንግሥቱ ተረጋግጦለታል፡፡ በኮንትራት በቤት ሠራተኝነት ወደ አረብ አገሮች የሚሄዱ ኢትዮጵያዉያን የሚደርስባቸዉ በደል ከጊዜ ወደ ጊዜ መባባሱ ይሰማል።   ኢትዮጵያውያኑ ላይ ከፍተኛ  የሆነ አካላዊና ሥነ ልቦናዊ  ጉዳት እየደረሰ ነው። ለዚህም በዋነኛነት ማሳያ የሚሆነው በተለያዩ የዓረብ አገሮች በቤት ሠራተኛነት በሚሄዱት እህቶቻችን ላይ የሚታየው የሞት፣ የአካል መጉደል፣ የመደፈርና ያለደመወዝ ማባረር ጥቂቶች ናቸው፡፡ በዚህ ዓመት እንኳን ከዓለም ደቻሳ ጀምሮ  በድብደባ ህይወታቸውን ያጡትን  ለከፍተኛ የአካል ጉዳት የተዳረጉትን የተደፈሩትን ከፎቅ የተወረወሩትን ለአእምሮ መቃወስ የተዳረጉት የትየለሌ ናቸው ኢትዮጵያዉያን የኮንትራት ሰራተኞች በአሰሪወቻቸው የሚደርስባቸውን ጥቃት ታዋቂ የሳዉዲ ጋዜጦች ሳይቀሩ በዝርዝር እየዘገቡት ነው፡፡

የወገኖቻችን እንግልት የሚጀምረው አገራቸው ላይ ነው፡፡ የሳዑዲ ዓረቢያ ዜግነት ያላቸው ኢትዮጵያውያንም በዜጎቻችን ላይ ክብራቸውን ጭምር የሚነካ ተግባር የሚፈጽሙ አሉ፡፡ በተለያዩ የአገሪቱ ክልሎች በደላላዎች እየተደለሉ ከየቀያቸው እየተፈናቀሉ ዜጎቻችን ለጉዳት እየተዳረጉ ነው፡፡ ሁሉም ነገር አልጋ ባልጋ እንደሆነና ወርቅ ተነጥፎ እንደሚጠብቃቸው በመስበክ ወጎኖቻችንን እያስጨረሱ ነው፡፡ ከእነዚህ ደላሎች በስተጀርባ የመንግስት እጅ አለበት መንግሥት ዜጎችን ከመጠበቅና ካለበት ኃላፊነት አንጻር እሱም ተጠያቂ ነው፡፡ ዕድሜያቸው እንዳልሞላ እየታወቀ ከ13-15 ዓመትን ልጅን 23-26 ዓመት በማለት  በማጣራትና አይቶም መገመት ሲቻል ፓስፖርት ይሰጧቸዋል የሚያስደነግጥ ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ወደ ሳዑዲና ኩዌት ለመሄድ የሚመጡት መጻፍ፣ ማንበብ የማይችሉና መታወቂያና ፓስፖርት መሆኑን መለየት የማይችሉ ናቸው፡፡ ፓስፖርት እስከሚያወጡና የሕክምና ምርመራ እስከሚደረግላቸው ድረስ ብዙ ችግሮችን ያሳልፋሉ ሁሉም ነገር ተሳክቶላቸው እስከሚሄዱ ድረስ የደላሎቹ የወሲብ መፈጸሚያ ይሆናሉ፡፡ የጤና ምርመራ ሲደረግላቸውም የHIV ተጠቂ ሆነው ይገኛሉ ውጤታቸው ሲነገራቸው እንደ ውርደት ስለሚቆጥሩት ተመልሰው ወደቀያቸው መግባትን ይተዉና ራሳቸውን በመሸጥ ለመተዳደር ይሞክራሉ፡፡ በሽታውንም ያስተላልፋሉ ላልተፈለገ እርግዝና ለ አደንዛዥ ዕፆች ተጋላጭ እየሆኑ ነው፡፡


የጤና ምርመራ ውጤቱን አግኝተው ከተጓዙ በኋላ በተቀባይ አገሮችም ችግር ይደርስባቸዋል፡፡ እዚያ ሲመረመሩ ብቁ አይደላችሁም ተብለው እንዲመለሱ ይገደዳሉ ወይም የት እንዳሉና ማን እንደቀጠራቸው፣ ስንት ቤተሰብ ያለበት ቤት እንደሚገቡ   በስንት እንደተቀጠሩ፣ ቀጣሪዎች ለሕገወጦች ከፍለናል የሚሉት ገንዘብ ስንት እንደሆነና ከሄዱ ከስንት ጊዜ በኋላ ደመወዛቸውን እንደሚያገኙ አያውቁትም፡፡  ዱባይ ከደረሱ በኋላ ወደ አፍጋኒስታንና ኢራን ሳይቀር ለቤት ሠራተኝነት ያግዟቸዋል፡፡ ወይም ዱባይ አየር መንገድ ደርሰው የሚቀበላቸው ሰው ባለማግኘት አየር ማረፊያው አካባቢ ሜዳ ላይ ለመዋልና ለማደር፣ ለምኖ ለመብላትም የተገደዱ በርካቶች ናቸው፡፡ እነዚህ ልጆች ወዴት እንደሚሄዱና ለምን እንደሚሄዱ እነሱ ብቻ ሳይሆኑ መንግሥት ራሱ ማወቅ ነበረበት፡፡ የዜጎቹን መብት የሚያስከብር መንግስት የለንም በዚህ የተነሳ ዜጎች በተለያዩ መንገዶች በሕገወጥ መንገድ እየወጡ ነው፡፡ የሚደርስባቸውን አደጋ መንግሥት ጠንቅቆ ያውቀዋል፡
 
የዚህ ምክንያት ብዙ ነው፡፡ አንዱና ዋነኛው ቁጥጥሩና ክትትሉ በአግባቡ አለመቃኘቱ ነው፡፡ ዜጎች በየትኛውም ቦታ የመዘዋወር ሕገመንግሥታዊ መብት አላቸው፡፡ ነገር ግን በተለይ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ የሚደረገው ጉዞ ለሥራ መሆኑን መንግሥት ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ ጉዞው በህጋዊ መንገድ መሆን ሲገባው፣ በተለያየ መንገድ የሚመጣላቸውን ቪዛ ሕጋዊ ሳያስደርጉና ሳይመዘገቡ ዝም ብለው ነው የሚሄዱት፡፡ ይኽ ደግሞ በውጭ አገር ያሉ ሕገወጦች ቪዛዎችን እያወጡ ወደ ኢትዮጵያ ሲልኩ እዚህ ያሉት ሕገወጦች ተቀብለውና በሕገወጥ መንገድ ለመለመሏቸው ዜጎች ይሰጣሉ፡፡ በዚህ መካከል ሕገወጦቹ እየተጠቀሙባቸው ይገኛሉ፡፡  

በኢትዮጵያ የኩዌት ኤምባሲ ከሚሠሩ የበታች ሠራተኞች ጋር በሚደረግ የምስጢር ግንኙነት ሕጋዊ ሥርዓቱን በሚቃረን መልኩ እየተሠራ ነው፡፡ በመሆኑም ሕጋዊዎቹ ኤጀንሲዎች ሥራቸው እየተዳከመ ነው፡፡ መንግስት ባለበት አገር  ሕግ እየተጣሰ በሕጋዊ መንገድ በሚላከው ቪዛ ዜጎች በሕገወጥ መንገድ እየሄዱ ነው፡፡  
 
በሳዑዲ ዓረቢያ ያሉ የኢትዮጵያ ቆንስላዎች ወደ ሳዑዲ የሚላኩ ሠራተኞች ስለሚያገኙት ደመወዝ መወሰን የሚችሉት እነሱ እንደሆኑና እጅግ በወረደ ደመወዝ እንደሚያስቀጥሩ መረጃ አለ፡፡ በኩዌትና በሳዑዲ ዓረቢያ  በተለይ ጅዳ ላይ ኤምባሲው የሰው ኃይልን በርካሽ ዋጋ ሊያቀርብ እንደሚችል በአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን እያስነገረና በጋዜጣ ላይ ማስታወቂያው እየወጣ ነው፡፡ ተልዕኮአቸውና ኃላፊነታቸው አይደለም፡፡ በዚህ ጉዳይ የሚሳተፉ የኤምባሲ ሠራተኞች አሉ፡፡ በኩዌት አካባቢም ከአሠሪዎቻቸው  ሸሽተው ከለላ ለማግኝት  ወደ ኤምባሲ ለመጠለል ስሄዱ ኤምባሲው  ውስጥ ባሉ ሰራተኞች አማካይነት ለሌላ አሠሪ አሳልፈው እንደሚሸጧቸው ነው  መረጃዎች የሚያመለክቱት፡፡ ይህንን ጉዳይ ለማስቆም የተንቀሳቀሱትን ወገን ወዳድ ዜጎች  በመንግስት ባለስልጣናት ታፍነዋል፡፡
  
በአሁኑም ጊዜ ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ በቀን ከአንድ ሺሕ እስከ አንድ ሺሕ አምስት መቶ ይሄዳሉ፡፡ ተቀባይ አገሮች ከሌሎች ሠራተኛ አቅራቢ አገሮች ጋር ያላቸው ግንኙነት ጥሩ ስላልሆነ ፊታቸውን መሪና መንግስት ወደ ሌላት  ኢትዮጵያ አዙረዋል ምክንያቱም ሌሎች አገሮች የዜጎቻቸውን መብት እያስከበሩ ሰለሚልኩ በአሁኑ ጊዜ ብዙ አገሮች ወደ መንግስት አልባዋ ኢትዮጵያ ትኩረት እያደረጉ ነው፡፡
 

ለምሳሌ ፊሊፒንን  ብንወስድ በዱባይ የሚገኘው ኤምባሲያቸው ጉዟቸውን ሳያፀድቅ አገራቸውን ለቀው አይወጡም፡፡ የአገራቸው መንግሥትም ማንኛውም የቤት ሠራተኛ ሆኖ የሚሄድ ዜጋው ከ450 ዶላር በታች ተከፋይ ሆኖ እንዳይጓዝ በሕግ ደንግጓል፡፡ ችሎታና የትምህርት ደረጃቸውን በሚመለከት የሚሞሉት የቅጥር ፎርም ትክክለኛና እውነተኛ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ለሚያጋጥሟቸው አስከፊ ችግሮች፣ ለሚደርስባቸው ከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ረገጣና የጉልበት ብዝበዛ መነሻ የሴቶቹ የአገሩን ባህልና አኗኗር ዘይቤ አለማወቅና ለሥራቸው የሚያስፈልጋቸውን ሥልጠና አለማግኘት ነው፡፡  እንደ ልብስ ማጠቢያ ወይም ምግብ ማብሰያ ባሉ ማሽኖች ግራ ይጋባሉ፡፡ ስለሚቀጠሩበት ቤት ሁኔታ፣ የቤተሰብ ብዛት ሌላም ሌላም አንድም የሚያውቁት ነገር ሳይኖር ከአገር ይወጣሉ፡፡ በተለይም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እንደሚታየው ወደ አረብ አገሮች በመሔድ ላይ ያሉት ለአዲስ አበባ እንኳ እንግዳ የሆኑ ከገጠር አካባቢ የሚመጡ ልጆች ናቸው፡፡
 
በሌላ በኩል የሚቀጥራቸው እንዲገኝ ሲባል የኢትዮጵያውያኑ የቅጥር ፎርም ችሎታቸው ምንም ይሁን ምን ሁሉንም ዘመናዊ የቤት ውስጥ መገልገያ ማሽን መጠቀም እንደሚችሉ፤ ማንኛውንም ሥራ ለመሥራትም ብቃት እንዳላቸው ተደርጎ ይሞላል፡፡ ይህን ከፍተኛ ቁጥር የተመለከቱ ዱባይ ውስጥ የሚገኙ ህንድና ፓኪስታናዊ ደላሎች አማርኛ ለምደው ሥራቸውን እያቀላጠፉ ኢትዮጵያውያኑ በወር የሚከፈላቸው 135 ዶላር ሲሆን፣ ኤጀንሲዎች አንዲት ኢትዮጵያዊትን በማስቀጠር የሚያገኙት 500 አልያም 550 ዶላር ነው፡፡ በተቃራኒው አንዲት ፈሊፒን የቤት ሠራተኛን በማስቀጠር ኤጀንሲዎች ከ2700 ዶላር በላይ ያገኛሉ፡፡ ‹‹አንዲት ፊሊፒን ለሚቀጥር ኢትዮጵያዊ ይመረቅለታል›› የሚሉ ማስታወቂያዎች በተለያዩ የሥራ ማስታወቂያ ጋዜጦችና ድረ ገጾች ላይ መመልከትም የተለመደ ሆኖአል፡፡
 
 እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ

 


 

No comments:

Post a Comment