Tuesday 18 September 2012

‹‹ኢሕአዴግ ሲወድቅ ደውሉልን››


በተደጋጋሚ የገለጽነውና የምንገልጸው ቁም ነገር አለ፡፡ ገዢው ፓርቲ ኢሕአዴግ ድክመት አለበት ማለት ተቃዋሚዎች ግን ጠንካሮች ናቸው፤ ትክክል ናቸው ማለት አይደለም፡፡ ተቃዋሚዎች ደካሞች ናቸው ማለት ደግሞ ገዢው ፓርቲ ግን ጠንካራና ጎበዝ ነው ማለት አይደለም፡፡ ሁሉም በየራሳቸው ማንነትና ተግባር መገምገምና መገለጽ አለባቸው፡፡ ያንዱ መደመር ለሌላው መቀነስ ነው ማለት አይደለም፡፡ ያንዱ መቀነስ ደግሞ ለሌላው መደመር መሆን አይደለም፡፡ ጉዳዩ የሥራህ ያውጣህ ጉዳይ ነው፡፡

ይህንን ካልን ዘንድ በአሁኑ ጊዜ በኅብረተሰባችን ውስጥ ስለሚንሸራሸረው፣ ስለሚነገረውና ስለሚወራው ነገር በግልጽ እናውራበት፤ በግልጽ እንነጋገርበት፡፡


ገዢው ፓርቲ ኢሕአዴግን በሚመለከት የተለያየ አመለካከት አለ፡፡ ኢሕአዴግ ጥሩ እየሠራ ነው፤ ለዘለዓለም ይኑር የሚል አለ፡፡ ኢሕአዴግ በዚህ በዚህ ጥሩ እየሠራ ነው፤ በዚህ በዚህ ደግሞ ደካማ ነው የሚልም አለ፡፡ የለም ኢሕአዴግ ጭራሽ መጥፎ ነው፤ ብሎ ጥሩ ነገር አታሰሙም የሚልም አለ፡፡ ኢሕአዴግ ባይኖር ኖሮ ፀሐይ በኢትዮጵያ አትወጣም ነበር፤ የሚል ጽንፈኛ ደጋፊ እንዳለ ሁሉ፣ ኢሕአዴግ ሥልጣን ባይዝ ኖሮ በኢትዮጵያ ውስጥ ጨለማ የሚባል ነገር አይኖርም ነበር፤ ብሎ ኢሕአዴግን የሚቃወምና የሚጠላ ጽንፈኛም አለ፡፡ እኛ ራሳችንም ኢሕአዴግ የሠራቸው አዎንታዊና የሚያስመሰግኑ ነገሮች አሉ፤ የፈጸማቸው በርካታ ጉድለቶችና ድክመቶችም አሉ ባዮች ነን፡፡ ሺሕ ጊዜ የጻፍንበት ጉዳይ ነው፡፡ የሚያስመሰግኑትም፣ የሚያስጠይቁትም አቋሞችና አመለካከቶች፣ ተግባሮችም አሉት እንላለን፡፡

ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ድርጅቶችን በሚመለከትስ?
ተቃዋሚ ድርጅቶች በግልጽ ሊነገራቸውና ሊያውቁት የሚገባ በግልጽ እየተንጸባረቀ በመምጣት ላይ ያለ የሕዝብ አመለካከት አለ፡፡ አመለካከቱም ኢሕአዴግስ ቢወድቅ፣ ኢሕአዴግን ተክተው ኢትዮጵያን የሚመሩ ተቃዋሚ ድርጅቶችና አመራሮች አሉ ወይ? ለሚለው ጥያቄ፣ ‹‹የሉም!›› የሚል ስሜት በሕዝብ ውስጥ አለ፡፡

ኢትዮጵያ ውስጥ ሆነን በሕጋዊና በሰላማዊ መንገድ መታገል ይቻላል ብለው የሚያምኑ ተቃዋሚዎች አሉ፡፡ ሰላማዊና ሕጋዊ መንገድ መምረጣቸው ትክክል ነው፡፡ ያስመሰግናቸዋልም፡፡ በሕጋዊና ሰላማዊ መንገድ ውስጥ ሆነው አመርቂና ትክክለኛ ትግል ሲያካሒዱ ግን አይታዩም! አይሰሙም!

መንግሥት መጥፎ ነው፤ መንግሥት ስህተተኛ ነው፤ መንግሥት አገር እየሸጠ ነው ብሎ ገዥ ፓርቲውንና መንግሥትን መውቀስ ቀላል ነው፡፡ ከተቃዋሚዎች የሚጠበቀው ግን የመንግሥት የኢኮኖሚ ፖሊሲ አካሔድና ፖሊሲ ስህተት ነው፡፡ እኛ ሥልጣን ስንይዝ በተግባር ላይ የምናውለው ፖሊሲና ሕግ ይህን ይመስላል፤ የሚል አማራጭ ማቅረብ ነው፡፡ በሰብዓዊ መብት፣ በዴሞክራሲ፣ በፍትሕ፣ በዲፕሎማሲ ፕሮግራማችን፣ ስትራቴጂያችን ይህን ይመስላል ብሎ የኔ የተሻለ ነው ብሎ መሟገትና መታገል ከተቃዋሚዎች የሚጠበቅ ነው፡፡ ይህ ግን የለም፡፡

ከተቃዋሚዎች የሚጠበቀው ፕሮግራም፣ ስትራቴጂና ታክቲክ መንደፍና በእያንዳንዱ ሁኔታ ላይ አቋምን ግልጽ ማድረግ ብቻ አይደለም፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የራስን ፓርቲ ማጠናከር፣ ዴሞክራሲያዊ ማድረግ፣ ከሙስና ማጽዳት፣ ጉባኤዎች ማካሔድ፣ ምርጫን ማከናወን፣ አባላትን ማጥራት፣ መመልመል ወዘተ. ይጠበቃል፡፡ ይህም የለም፡፡

በተቃዋሚዎች በኩል ኢሕአዴግ እንዲወድቅ ፍላጎቱ አለ፡፡ ኢሕአዴግ እንዲወድቅ የሚያደርግ ትግል ግን በተቃዋሚዎች የለም፡፡ ሥልጣን የመያዝ ፍላጎት አለ፡፡ ሥልጣን ላይ የሚያወጣ ትግል ግን የለም፡፡ እየታየ ያለው፣ ‹‹ሕዝብ ይነሣሣና ኢሕአዴግን ይጣል፤ ኢሕአዴግ ሲጣልና ሲወድቅ ደውሉልን›› የሚል ነው፡፡ ያሳዝናል፡፡ ሐቁ ግን ይኸው ነው፡፡ ‹‹ኢሕአዴግ ሲወድቅ ደውሉልን››፡፡

በውጭ አገር ሰላማዊና ሕጋዊ የትግል መንገድ አንፈልግም የሚሉ ተቃዋሚዎችም አሉ፡፡ በዓለም አቀፍ ግፊትም ይሁን፣ በትጥቅ ትግልም ይሁን፣ እንደ ግብፅ፣ ሊቢያና ቱኒዚያ ሕዝብ በአመጽም ይሁን፣ ኢሕአዴግ ብቻ ይውደቅ የሚል አቋም ነው፡፡ ሻዕቢያም ይደግፍ፣ አልሻባብም ይደግፍ፣ የፈለገው ይደገፍ፣ ሥልጣን እስከተያዘ ድረስ መፈክሩ ‹‹የትም ፍጪው ሥልጣኑን አምጪው›› ነው፡፡

የሚገርመው ግን ይህም ሆኖ ሥልጣኑን ለመያዝ ፍላጎት ያላቸው መስዋዕትነት ለመክፈል ዝግጁ አይደሉም፡፡ ትጥቅ ትግሉን እንመራዋለን፤ ነገር ግን በትርፍ ጊዜ ነው የምንመራው እንጂ ዋናው ሥራችን በአሜሪካ ዩኒቨርሲቲ ማስተማር ነው ይላሉ፡፡ የትጥቅ ትግል መምራት በትርፍ ጊዜያችን የምናደርገው ነው ይላሉ፡፡ ሌሎቹ ደግሞ ኢሕአዴግ እንዲወድቅ እንፈልጋለን፤ እንመራለን፤ ነገር ግን የድኅረ ምረቃ ትምህርት መማር ስለምንፈልግ ሙሉ ጊዜያችንን በአገር ውስጥ ሆነን ማሳለፍ አይመቸንም ይላሉ፡፡

መልዕክታቸው ባጭሩ ሲቀመጥ እንዲህ ይመስላል፡፡ ‹‹እናንተ ታገሉ፤ ኢሕአዴግን ጣሉ፤ ከጣላችሁ በኋላ እኛ ሥልጣኑን እንድንይዝ ደውሉ፡፡››

ስትራቴጂው፣ ታገሉ! ጣሉ! ደውሉ! ነው፡፡ ይህ ቀልድ ነው፡፡ ይህ ፌዝ ነው፡፡ አገራችን ኢትዮጵያ ጠንካራ የፖለቲካ ፓርቲዎች ያስፈልጓታል፡፡ ጠንካራ ገዥ ፓርቲና ጠንካራ ተቃዋሚዎች ሲኖሩ ሕዝብ አማራጭ ይኖረዋል፡፡ ዴሞክራሲም ይጠናከራል፡፡ ዋስትናም ያገኛል፡፡

ጠንካራ ተቃዋሚዎችና ገዥ ፓርቲ ይኑር ስንል ግን መመዘኛው ቁም ነገር፣ ሕዝብን የሚያገለግሉና የሚመሩ፣ ለአገርና ለሕዝብ ብለው ዋጋ የሚከፍሉ መሪዎችና አባላት ያሉበት ፓርቲ ማለታችን ነው፡፡

እኔ እበልጥ፣ እኔ እሻል ብለው ተወዳድረው ሕዝብ የሚመርጣቸው እንጂ፤ ትግሉን ረስተው ሥልጣንን የሚቋምጡ ፓርቲዎችና መሪዎችን አንፈልግም፤ አንሻም፡፡

ስለዚህ? ስለዚህማ ተቃዋሚዎች ሆይ! እባካችሁን ስህተታችሁን አርሙ፤ ገምግሙ፤ ውስጣችሁን ፈትሹ፤ ዴሞክራሲያዊ የውስጥ አሠራርና አመራር ይኑራችሁ፡፡ ለሕዝብ ጥቅም ዋጋ ክፈሉ፡፡ ያኔ ተወዳደሩ፤ የተሻለውን መምረጥ ለሕዝቡ ተዉ፡፡ ሁሉም ፓርቲ ጠንካራ ከሆነ ምርጫውም ስኬታማ ይሆናል ብላችሁ እመኑ፡፡

ከዚህ ውጭ ግን መፈክራችሁን ካላስተካከላችሁና አሁንም ‹‹ኢሕአዴግ ሲወድቅ ደውሉልን›› የምትሉ ከሆነ፣ የሕዝቡ መልስ፣ ‹‹እውነተኛ ተቃዋሚዎች መሆን ስትጀምሩ ደውሉልን›› የሚል ይሆናል፡፡ ሕዝቡ ግን አይደውልም፡፡

Reporter News Paper

No comments:

Post a Comment