Sunday 14 October 2012

የግል ባንኮች ለቦንድ ግዥ ከ14 ቢሊዮን ብር በላይ አውጥተዋል

የ27 በመቶ ቦንድ ግዥ ጫና ፈጥሮባቸዋል
 
የግል ባንኮች ከሚያበድሩት ገንዘብ ላይ 27 በመቶ ለቦንድ ግዥ እንዲያውሉ መመርያ ከወጣ ወዲህ በ2004 በጀት ዓመትና በ2005 የመጀመርያው ሩብ ዓመት ብቻ ከ14 ቢሊዮን ብር በላይ ለብሔራዊ ባንክ ገቢ አድርገዋል፡፡ የአገሪቱን የፋይናንስ ተቋማት የ2004 በጀት ዓመት አጠቃላይ አፈጻጸም የሚያመለክተው መረጃ የግል ባንኮችን የሚያስገድደው መመርያ በበጀት ዓመቱ ማበደር ይችሉ የነበረውን ያህል እንዳያበድሩ ተፅዕኖ እንዳሳደረባቸው አመልክቷል፡፡ ባንኮቹ በ2004 በጀት ሙሉ ዓመት 12.5 ቢሊዮን ብር ለቦንድ ግዥው ገቢ ሲያደርጉ፣ በ2005 የመጀመርያዎቹ ሦስት ወራት ደግሞ ከሁለት ቢሊዮን ብር በላይ እንዳስገቡ የተገኘው መረጃ ይጠቁማል፡፡

በመመርያው መሠረት አምና አሥራ አራቱም የግል ባንኮች ካበደሩት 34.9 ቢሊዮን ብር ላይ የተቀነሰው 27 በመቶ ከሰጡት ብድር መጠን ጋር ሲነፃፀር አንድ ሦስተኛውን እጅ ይበልጣል፡፡ እንደ ኢኮኖሚ ባለሙያዎች ገለጻ፣ በበጀት ዓመቱ የግል ባንኮች ከእያንዳንዱ ብድር ለብሔራዊ ባንክ በሦስት ከመቶ ወለድ እንዲያስገቡ የሚያዘው የ27 በመቶ ግዳጅ ባይኖር፣ በበጀት ዓመቱ ካበደሩት ብድርና ካገኙት ትርፍ በላይ ያገኙ ነበር፡፡ እነዚሁ ኢኮኖሚ ባለሙያዎች እንደሚሉት፣ ባንኮቹ በመመርያው መሠረት ባንኮቹ ከየብድሩ በሦስት በመቶ ወለድ እያስቀመጡ በሄዱ ቁጥር ይኖራቸው የነበረውን ተቀማጭ ገንዘብ እየበላ ስለሚሄድ ለባንኮቹ የወደፊት አደጋ ሊሆን እንደሚችልም ያስጠነቅቃሉ፡፡ ከእያንዳንዱ ብድር 27 በመቶ ተቀማጭ እንዲያደርጉ የሚያስገድደው መመርያ መንግሥታዊውን የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የማይመለከት መሆኑ ደግሞ፣ በኢንዱስትሪው ውስጥ ያለውን የውድድር ሜዳ አጥብቦታል ይላሉ፡፡


የ27 በመቶ ቦንድ ግዥው እጅግ አሳሳቢ መሆኑን የሚጠቅሱት የኢኮኖሚ ባለሙያዎች፣ ከግል ባንኮች የሚሰበሰበው 27 በመቶ እየተሰጠ ያለው ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ነው ይላሉ፡፡ የሌሎቹን እየተቀበለ እሱ ገንዘቡን በሙሉ ይወስዳል፡፡ ይህንን ገንዘብ ወስዶ መንግሥት ለሚያምንባቸው ትልቅ ፕሮጀክቶችና ለመንግሥት ድርጅቶች ብድር ይሰጣል ብለው፣ ይህ ገንዘብ መሄድ የነበረበት ግን አዋጪ ሥራ ወደሚሠሩ የግሉ ዘርፍ ተቋማት ነበር የሚል እምነት አላቸው፡፡

አያይዘውም በአሁኑ ወቅት ትልቁ ችግር መንግሥት ካላተመ በስተቀር ገንዘብ የሌለው መሆኑ ነው ይላሉ፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የሚሰበሰበው ገንዘብ ለትላልቅ ፕሮጀክቶች በብድር እየተሰጠ ስለሆነ ነው፡፡ አንዳንድ የግል ባንኮች ያለባቸውን የገንዘብ እጥረት ለማስታገስ ለከፍተኛ ለገንዘብ አስቀማጮች በድርድር እስከ ስምንት በመቶ ወለድ ሲከፍሉ እየታየ ነው፡፡ የባሰባቸው አሥር በመቶም እየከፈሉ ገንዘብ ለማሰባሰብ እየሞከሩ ያሉት በየብድሩ የሚቆረጥባቸው 27 በመቶ በፈጠረው ጫና ምክንያት መሆኑንም ያስረዳሉ፡፡

ሌላ የባንክ ባለሙያ ደግሞ ባንኮቹ በአምስት በመቶ ወለድ በቂ ገንዘብ ማሰብሰብ አልቻሉም፡፡ ምክንያቱም በቂ ገንዘብ ባለመኖሩ ነው ይላሉ፡፡ የግል ባንኮች የገንዘብ ፍላጐት እጅግ በጣም እያደገ በመምጣቱና 27 በመቶ የቦንድ ግዥው በፈጠረባቸው ጫና ገንዘቡ ከቋታቸው ቶሎ ቶሎ ስለሚወሰድ፣ በከፍተኛ የወለድ ምጣኔ ከአስቀማጮች ጋር ወደመደራደር እየወሰዳቸው መሆኑን ይናገራሉ፡፡ ባንኮቹ በዚህ አካሄድ ከቀጠሉ የወደፊት ህልውናቸው አስጊ መሆኑንም አስታውሰዋል፡፡ ዓለም ባንክና አይኤምኤፍ ይህንን እየተቃወሙ ነው፡፡ የግል ዘርፉ እየተጐዳ በመሆኑ አቅም እያነሰው ነው ይላሉ፡፡ ነገር ግን አጥጋቢ መልስ አልተገኘም ያሉት እኚሁ ባለሙያ፣ መንግሥት ይህንን የ27 በመቶ ግዳጅ ማንሳት አለበት፣ ካልቻለ ደግሞ የግል ባንኮች ህልውና አደጋ ላይ መውደቁ አይቀርም ብለዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ ውስጥ ሦስት መንግሥታዊና 14 የግል ባንኮች በመሥራት ላይ ይገኛሉ፡፡ በቅርቡ ወደገበያ የገባውን ደቡብ ግሎባል ባንክና በያዝነው ወር ወደ ተግባራዊ ሥራ ይሸጋገራል ተብሎ የሚጠበቀው እናት ባንክ ሲታከሉ በአጠቃላይ በአገሪቱ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ባንኮች ቁጥር ወደ 19 ይደርሳል፡፡ የሁሉም የንግድ ባንኮች እንቅስቃሴ በየዓመቱ ዕድገት እየታየበት ቢሆንም፣ የግል ባንኮች የ27 በመቶ የቦንድ ግዥ መመርያ በተወሰነ ደረጃ ባይገታቸው ኖሮ እያገኙ ከሚገኘው በላይ የትርፍ ተጠቃሚ ይሆኑ እንደነበር ይናገራሉ፡፡

በ2004 የበጀት ዓመት አጠቃላይ የአገሪቱ የንግድ ባንኮች እንቅስቃሴን የሚያመለክተው መረጃ ሁሉም ባንኮች ከአንድ ዓመት በፊት አግኝተውት ከነበረ ትርፍ በላይ አግኝተዋል ይላል፡፡ የሁሉም የግልና የመንግሥት ባንኮች በ2004 በጀት ዓመት ከታክስ በፊት 11.6 ቢሊዮን ብር ትርፍ አግኝተዋል፡፡ ይህ የትርፍ መጠን ካለፈው ዓመት በጀት ዓመት ጋር ሲነፃፀር በአማካይ 20 በመቶ ዕድገት የተገኘበት ነው፡፡

ሁሉም የግል ባንኮች በጥቅሉ 34.9 ቢሊዮን ብር ብድር ሲሰጡ፣ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 54.9 ቢሊዮን ብር፣ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ 14.9 ቢሊዮን ብር በማበደር ከመንግሥት ባንኮች ቀዳሚውን ደረጃ የያዙ ሲሆን፣ የኮንስትራክሽንና ቢዝነስ ባንክ ደግሞ 2.05 ቢሊዮን ብር ማበደር እንደቻለ መረጃው ያሳያል፡፡ ሦስቱ የመንግሥት ባንኮች በጠቅላላው 71.9 ቢሊዮን ብር ማበደር ችለዋል፡፡ ይህ በበጀት ዓመቱ የመንግሥትም ሆነ የግል ባንኮች ካበደሩት 106 ቢሊዮን ብር ውስጥ የሦስቱ መንግሥታዊ ባንኮች ድርሻ 70 በመቶ ደርሷል፡፡

በ2004 ዓ.ም. አሥራ አራቱም የግል ባንኮች ማበደር የቻሉት 34.93 ቢሊዮን ብር ሲሆን፣ ከባንኮቹ ውስጥ ከፍተኛውን ብድር የሰጠው ዳሸን ባንክ አምና ያበደረው 8.04 ቢሊዮን ብር ነበር፡፡ ከዳሸን ቀጥሎ ያለው አዋሽ ባንክ 5.5 ቢሊዮን ብር፣ ሕብረት ባንክ ደግሞ 4.08 ቢሊዮን ብር ብድር ሰጥተዋል፡፡ የግል ባንኮች የትርፍ መጠን ሲታይም ከታክስ በፊት ከተመዘገበው 3.5 ቢሊዮን ብር ውስጥ ዳሸን ባንክ 897 ሚሊዮን ብር፣ አዋሽ 543 ሚሊዮን ብር፣ ወጋገን 415 ሚሊዮን ብር፣ ሕብረት 413 ሚሊዮን ብር፣ ንብ 390 ሚሊዮን ብር፣ አቢሲኒያ 313 ሚሊዮን ብር በማትረፍ ቅደም ተከተሉን ይዘዋል፡፡

በአሁኑ ጊዜ የአገሪቱ የፋይናንስ ተቋማት አጠቃላይ የሀብት መጠን 271.6 ከመቶ ደርሷል፡፡ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር ብልጫ ያለው ቢሆንም፣ የተቀማጭ ገንዘባቸው ዕድገት መጠን ግን አስገራሚ እየሆነ ነው፡፡ ሆኖም የአንዳንድ ባንኮች የተቀማጭ ገንዘብ መጠን እየቀነሰ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡

በፋይናንስ ኢንዱስትሪው ባንኮች ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በከፍተኛ ደረጃ ቅርንጫፎቻቸውን እያስፋፉ መሆናቸውን ዓመታዊው የፋይናንስ ተቋማት መረጃ ያሳያል፡፡ ባለሙያዎች እንደሚያመለክቱት፣ ባንኮቹ በደንበኞቻቸው አማካይነት የተቀማጭ ገንዘባቸውንም በማብዛት ተጠቃሚ ለመሆን እንደ አንድ አማራጭ የተጠቀሙት ቅርንጫፎቻቸውን በማበራከት በመሆኑ፣ ይህንን ስትራቴጂ ከዳር ለማድረስ ባለፉት 17 ዓመታት ባልታየ ሁኔታ ሁሉም ባንኮች በርካታ ቅርንጫፎች የከፈቱበት ጊዜ ያለፈው ዓመት ነው፡፡ 970 የነበሩት የሁሉም ባንኮች ቅርንጫፎች 1,246 ደርሰዋል፡፡

እስከ መስረከም 30 ቀን 2005 ዓ.ም. ድረስ ያለው መረጃ የሁሉም የአገሪቱ ባንኮች ቅርንጫፎች ቁጥር 1,255 መድረሱን ያመለክታል፡፡ ይህም ባለፈው ዓመት ከነበራቸው የቅርንጫፎች ብዛት ከ40 በመቶ በላይ ጭማሪ ያሳያል፡፡ ከ2003 ዓ.ም. በፊት በነበረው ጊዜ በየአንዳንዱ ዓመት ይህን ያህል ቁጥር ያለው ቅርንጫፍ በአንድ ዓመት ውስጥ የከፈቱበት ጊዜ አልነበረም፡፡ በበጀት ዓመቱ ሁሉም ባንኮች ካሉዋቸው 1,255 ቅርንጫፎች ውስጥ 576 የግል ባንኮች ይዞታዎች ሲሆኑ፣ 650 የሚሆኑት ደግሞ የሦስቱ የመንግሥት ባንኮች ቅርንጫፎች ናቸው፡፡ ከዚህ ውስጥ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 540 ቅርንጫፎች በመክፈት ቀዳሚውን ደረጃ ይዟል፡፡

ከግል ባንኮች 85 ቅርንጫፎችን በመክፈት አዋሽ ባንክ ሲጠቀስ፣ ዳሸን ባንክ 71 ላይ ደርሷል፡፡ የኢንዱስትሪው የሰው ኃይል ቁጥርም ከዓመት ዓመት እየጨመረ ሲሆን፣ በ2004 በጀት ዓመት መጠናቀቂያ ሁሉም ባንኮች 34,331 ሠራተኞችን ይዘዋል፡፡ ከዚህ ውስጥ የግል ባንኮች 18,526 ሠራተኞች ነበሯቸው፡፡ ከሦስቱ የመንግሥት ባንኮች ብልጫ በመውሰድ ሠራተኞችን መቅጠር ችለዋል፡፡ ሦስቱ የመንግሥት ባንኮች 15,805 ሠራተኞችን የያዙ መሆኑም ታውቋል፡፡

ኢትዮጵያ ውስጥ የግል ባንኮች ዘርፉን ከተቀላቀሉ ወዲህ ላለፉት 14 ዓመታት በግል ባንኮች ውስጥ ያለው የተቀማጭ ገንዘብ (Deposit) እየቀነሰ መምጣቱን የአክሰስ ካፒታል ጥናት ይጠቁማል፡፡ በባንክ ኢንዱስትሪው ውስጥ የተቀማጭ ገንዘብ በዋነኝነት የዘርፉ ቁልፍ አንቀሳቃሽ ቢሆንም፣ እ.ኤ.አ. በ2011 ከነበረበት 36 ከመቶ ቀንሶ በ2012 ከ24 በመቶ በታች መውረዱን ያሳያል፡፡

ከወራት ወዲህ ባልተጠበቀ ሁኔታ የግል ባንኮች የተቀማጭ የገንዘብ መጠን ከ20 እስከ 25 ከመቶ በታች ሲቀንስ ታይቷል፡፡ ለተቀማጭ ገንዘብ መጠን ማሽቆልቆል ዋናው ምክንያቱ የመንግሥት የገንዘብ ፖሊሲ እየጠበቀ መምጣትና የመንግሥት ባንኮች እየተስፉፉ በመምጣታቸው የተነሳ በተፈጠረው ጠንካራ የውድድር ግፊት ነው፡፡ የተቀማጭ ገንዘብ እየቀነሰ መምጣቱ የግል ባንኮች ብድር የማቅረብ አቅም ላይ ጋሬጣ እየፈጠረ መሆኑንም የአክሰስ ጥናት ይጠቁማል፡፡

የአምስት ዓመቱን የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድን ተፈጻሚ ለማድረግ ከሚያስፈልገው ገንዘብ ውስጥ 345 ቢሊዮን ብር የሚሆነው ሊሰበሰብ የታቀደው ከአገሪቱ የፋይናንስ ኢንዱስትሪ ነው፡፡ የሌሎች አገሮች ልምድ እንደሚጠቁመው፣ ባንኮች መንግሥታት ፋይናንስ እንዲያገኙ ትኩረት ላደረገባቸው ዘርፎች እንዲያበድሩ መመርያ ያወጣሉ እንጂ፣ ልክ ኢትዮጵያ ውስጥ እንደሚደረገው የግል ባንኮች በየወሩ ከሚበደሩት ላይ 27

No comments:

Post a Comment