Wednesday 10 October 2012

የመድረክ የዲሲ ጉባዔ በፖለቲካ ሂደትና አመራር ሲያተኩር፤ የተቃዋሚዎችን የሃሳብ አለመቻቻል ጠቆመ

የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ መድረክ በትናንትናውለት በዋሽንግተን ዲሲ ያካሄደው ህዝባዊ ስብሰባ የኢትዮጵያን የፖለቲካ ሂደትና አመራር ሲገመግም፤ በአንጻሩ ተቃዋሚዎች እርስ በርሳቸው ያላቸው ክፍፍል እየሰፋ መሄዱን ጠቁሟል።

በተለያዩ የዩናይትድ ስቴይትስ ግዛቶች ባለፉት ጥቂት ሳምንታት ውስጥ የመድረክ መሪዎች በዴንቨር፣ ሜኔሶታ፣ ሲያትልና ሌሎች ከተሞች ከኢትዮጵያዊያን ጋር ሲወያዩ ነው የቆዩት።

የእሁዱ የዋሽንግተን ዲሲ ጉባዔ አላማው በኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳዮች ከደጋፊዎችና ከሰፊው ማህበረሰብ ጋር ለመወያየት፣ ድርጅቱ ከነበረበት የተከፋፈለ የፓርቲ አደረጃጀት ወደ ግንባር መሸጋገሩ፣ በአጠቃላይ ለኢትዮጵያ የፖለቲካ እክሎች ድርጅቱ መፍትሄ ብሎ ያስቀመጣቸውን የፖሊሲና አስተዳድር አቅጣጫዎች ለመጠቆም ያለመ ነበር።

ከ350-400 የሚገመቱ ሰዎች በተሳተፉበት ህዝባዊ ስብሰባ የመድረክ አመራሮች አስቀድመው፤ የቀድሞው ኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ እረፍተን ተከትሎ በሀገሪቱ መጻኢ የፖለቲካ ጉዞ የየግልና የድርጅታቸውን አስተያየት ሰጥተዋል።


በኛ እምነት ከእንግዲህ የምናውቀው ኢህአዴግ አይኖርም። ተወደደም ተጠላም ስታትስኮው (ነባራዊ ሁኔታው) ተቀይሯል። ኢህአዴግ ያሉት አማራጮች ወይ ለውጡን የተገነዘበና የታሰበበት የማሻሻያ እርምጃዎች መውሰድ፤ ወይንም ደግሞ እነርሱ እንደሚሉት የታላቁ መሪያችን ራእይ አንለቅም እያሉ ነገሮችን እንደነበሩበት ለማስቀጠል መሞከር ነው” ብለዋል አቶ ስየ አብርሃ
በኢትዮጵያ የሚታየው የኢኮኖሚ እድገት የአሃዝ ጭማሪ እንጂ፤ የህዝቡን ኑሮ ያልለወጠ፣ ወይንም ማሻሻል ያልጀመረ ነው ሲሉ፤ የገዥው ፓርቲ ኢህአዴግን የምጣኔ ሀብት ፖሊሲ የተቹት ደግሞ አቶ ተመስገን ዘውዴ ናቸው። የምጣኔ ሀብት ቁጥጥሩ በጥቂት የመንግስትና የፓርቲ ድርጅቶች መኖሩ በዘለቄታ አገሪቱን እንደሚጎዳና የግሉን ዘርፍ ተወዳዳሪነት ያቀጨጨ ነው ብለዋል አቶ ተመስገን። ከሁሉም አሁን የአገሪቱን ህዝብ እየጎዳ ያለው፤ “የዋጋ ንረት ነው” ብለዋል አቶ ተመስገን።
የቆዩ የፖለቲካ ቁርሾዎች ያቆሰሏቸው ግለሰቦችና ቡድኖችም ነበሩ። በተለይ አቶ ስየ አብርሃ ንግግራቸውን ለማቅረብ ወደ መድረኩ ሲጋበዙ የተቃውሞ ድምጽ ተሰማ፤ ቤተሰቦቻችንና የትግል ጓዶቻችን አቶ ስየ በመሪነት በነበሩበት የኢህ አዴግ አስተዳድር ተገድለውብናል፣ እራሳችን ታስረናል፣ ጉዳት ደርሶብናል የሚሉ ድምጾች ተስተጋቡ

ከኢሀፓ ወጣቶች ሊግ አስቀድሞ አቶ ስየ ሲናገሩ የተቃወመው ወጣት ታዘበው አሰፋ ጥያቄውን አቀረበ።

“በሀገራቸው ውስጥ መኖር ሲችሉ፤ ጫካ ገብተው ለኢትዮጵያ አርሶ አደር መሬት ላራሹ ብለው የታገሉትን ሰዎች ደብዛቸውን አጥፍቷል [አቶ ስየ አብርሃ]”​​
አቶ ስየ አብርሃ መልሳቸውን ሲሰጡ፤ በኢህ አዴግ አስተዳድር ወቅት በሃላፊነት ሲሰሩ ለተፈጸሙ የመብት ጥሰቶችና አግባብነት የሌላቸው የህዝብን ጥቅም ያላስጠበቁ ውሳኔዎች “ሀላፊነት እወስዳለሁ” አሉ፤ የስልጣን ፍላጎት እንደሌላቸውና በአገራቸው ህዝቦችን የሚያገለግል ፍትሃዊና ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ከመገንባት ያለፈ ፍላጎት እንደሌላቸውም ተናገሩ።

በተለይ ከኢህ አፓ ጋር የነበረውን ታሪካዊ ደም አፋሳሽ ግጭት አስመልክተው በቀጥታ ሲናገሩም ሁላችንም “ተገዳድለናል? ተዋግተናል? ህይወት ጠፍቷል?” ካሉ በኋላ፤ ጥያቄያቸውን በአወንታ መልሰው “አዝናለሁ! ግን ከሁሉም ወገን ነው የጠፋው” ብለዋል።
አስቀድመው የትግራይ ክልል ፕሬዝደንት የነበሩት አቶ ገብሩ አስራት በተቃዋሚ ፖለቲካ የገቡበትን ምክንያት ሲያስረዱ የስልጣን ፍላጎት ወደ ተቃውሞ እንዳላስገባቸው ገልጸዋል።
የመድረኩ ዶ/ር መራራ ጉዲና ተከትለው ያለፉ ቁርሾዎች ላይ ዛሬም የምንነጋገር ከሆነ፤ እንደታሪክ መማሪያነታቸው ጥፋቶችን አምነን፣ የማስተካከያና እርስ በርስ መቀራረቢያ ድልድዮች ከሌሉ፤ የአገሪቱ የዴሞክራሲ ጉዞ ይስተጓጎላል ሲሉም አብራርተዋል


 

No comments:

Post a Comment