Sunday 28 October 2012

የንግግር ጥበብ

የንግግር ጥበብ አንድ ብዙ ማውራት የሚወድ ወጣት ወደ ፈላስፋው ሶቅራጥስ ዘንድ በመሄድ ‹‹የንግግር ጥበብ›› እንዲያስተምረው ይጠይቀዋል፡፡ ፈላስፋውም ‹‹አንተን የማስከፍልህ ሌሎች ከሚከፍሉት በእጥፍ ነው›› አለው፡፡ ወጣቱም በመደነገጥ ስሜት ‹‹እጥፍ የምታከፍለኝ ምክንያቱ ምንድን ነው?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ ሶቅራጥስም ‹‹አንተን የማስተምርህ ሁለት ዓይነት ጥበብ ነው፡፡ አንደኛው የንግግር ጥበብ ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ የማዳመጥ ጥበብ ነው፡፡ የሁለተኛው ግን ከመጀመርያዋ ይበልጣል በማለት መለሰለት፡፡

ማዳመጥ ትልቁ የንግግር ጥበብ ነው ፈጣሪ መናገር እንድንችል ምላስ ብቻ ሳይሆን ማዳመጥ እንድንችልም ጆሮ ሰጥቶናል፡፡ ንግግራችን የተሟላ እንዲሆን የግድ ማዳመጥ አለብን፡፡ ሌላው ቢቀር ተናግረን መሰማታችንን ማወቅ የምንችለው ሌላውን ማዳመጥ የቻልን እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ አንድ ምላስ ሁለት ጆሮ ሲሰጠን በራሱ ምክንያት አለው፤ ‹‹በመጠን ተናገሩ በብዛት አድምጡ›› የሚለውን መልእክት ለማስተላለፍ ብቻ ሳይሆን ብዙ ከመናገራችን በላይ ብዙ ማዳመጥ አለመቻላተን ታላቅ ጉዳት እንዳለውም ለማስገንዘብ ነው፡፡ በመልካም አስተሳሰብ የተሞላ አስተዋይ ሰው ከመናገሩ በፊት ያስባል፤ መቼ መናገርና መቼ ዝም ማለት እንዳለበትም ያውቃል፡፡ ሲናገር ‹‹በመጀመርያ ብዙ ከማውራት ይልቅ ብዙ ማዳመጥን እመርጣለሁ፡፡ መናገር ባስፈለገኝ ጊዜ ቃላቶቼ በከናፍርቶቼ በኩል ከመውጣታቸው በፊት ረጋ ብዬ እመዝናቸዋለሁ›› በማለት ተናግሯል፡፡

ማዳመጥ ለመስማት መፈለግ ነው  ፈላስፋውና የሒሳብ ሊቁ ብሌዝ ፓስካል ሲናገር ‹‹አንድ የደረስኩበት ነገር አለ፤ እርሱም የሰው ልጅ ሁሉም ክፋቶች የሚመጡት በውስጡ ዝም ማለት አለመቻሉ ላይ ነው፤›› ብሏል፡፡ ራሳቸውን የሚገዙ ሰዎች በማዳመጥ ችሎታቸው ከፍተኛ ደረጃ የደረሱ ናቸው፡፡ ጤናማ ቃልን የሚናገሩና አንደበታቸው ክፉ ቃል እንዳይወጣቸው የሚገቱ ሲሆኑ ዓለምን ለማሸነፍ ከመውጣታቸው በፊት ራሳቸውን ማሸነፍ የሚችሉ ናቸው፤ አስቀድመው ስለራሳቸው በደንብ ያውቁ ስለሆኑ የኩራትና የትዕቢትን ካባ ከላያቸው ላይ አውልቀው የጣሉ ናቸው፡፡ ሰዎችን በመስማትና በማዳመጥ መካከል ከፍተኛ ልዩነት አለ፡፡ ሰዎች ብዙ ሥልጣን እያገኙ ሲሄዱ ከእነርሱ በታች ያሉትን ለማድመጥ ትዕግሥት እያጡ ይሄዳሉ፡፡ የተደፈነ ጆሮ ለተዘጋ ጭንቅላት የመጀመርያው መገለጫ ነው፡፡

በተናገርነው እንጂ ዝም ባልነው መቼም አናፍርም
ብዙ ጊዜ እንወደዳለን ብለው የሚናገሩ ሰዎች ከመፈቀራቸው በተቃራኒ ጥላቻን አትርፈዋል፡፡ ፈላስፋው ፕሉታርክ እንዲህ ዓይነት ሰዎችን ሲገልጻቸው ‹‹በመናገራቸው ብዛት መወደድ የሚፈልጉ ይጠላሉ፤ እናስደስታለን ብለው ሲጠብቁ ይሰለቻሉ፡፡ እንደነቃለን ብለው ሲጠብቁ መሳቂያ ይሆናሉ፡፡ እንደነዚህ ዓይነት ሰዎች ወዳጆቻቸውን ሲጎዱ ጠላቶቻቸውን ደስ ያሰኛሉ፡፡ በመጨረሻም ራሳቸውን በራሳቸው ያጠፋሉ›› ብሏል፡፡

ከብዙ ንግግር ብዙ ስህተት ይገኛል እውነተኛ ማዳመጥ ውስጣዊ ነው፡፡ አንድ ንግግርን ከውስጣችን በደንብ ካዳመጥን ያዳመጥነው ከልባችን ጋር ይዋሃዳል፡፡ ፈላስፋው ፕሉታርክ ‹‹ማዳመጥ እውነተኛ የሆነ ሕይወት የመኖር ጥበብ ነው›› ብሏል፡፡
ማዳመጥ ጆሮን መክፈት ሳይሆን
ልብን መክፈት ነው፡፡ ማዳመጥ ከማይችል ሰው ጋር መወያየት እጅግ ከባድ ነው፡፡ ሁለት ሰዎች በደንብ መነጋገር ከፈለጉ ከሁለቱ አንደኛው ማዳመጥ ይኖርበታል፡፡ የብዙዎች ችግር ማዳመጥ አለመቻላቸው ሳይሆን እየተቻላቸው ሌሎችን ማዳመጥ አለመፈለጋቸው ነው፡፡ እንዲህ ዓይነት ሰዎች የሚያዳምጡ ይመስላሉ እንጂ የሚያዳምጡት ራሳቸውን ነው፡፡

የሥነ አእምሮ ሐኪሞች አእምሮው የታመመን ሰው ለማከም ትልቁ መንገድ መድኃኒተ መስጠት ወይም የሥነ ልቦና ምክርን መለገስ ብቻ ሳይሆን ልብን ሰጥቶ ማዳመጥ ከፍተኛ ቦታ እንዳለው ይናገራሉ፡፡ በአሁኑ ጊዜ ሰው ያጣው የሚያወራለትን ሳይሆን የሚያዳምጠውን ነው፡፡ ብዙ ሰዎች በልባቸው ውስጥ የሞላውን፣ ከወስጥ የሚሰማቸውን ጭንቀትና ሰላም ማጣት ሲገልጹ ልቡን ከፍቶ የሚያዳምጣቸው ሰው ይፈልጋሉ፡፡ ከመናገር በላይ ማዳመጥ የንግግር ጥበብ መሆኑን ማስተዋል ትልቅ ጥበብ ነው፡፡

ጥሩ የንግግር ችሎታ ያላቸው ሰዎች
ጥሩ የማድመጥ ችሎታ ያላቸው ናቸው፡፡
- ዳንኤል ዓለሙ (የምሕረት ልጅ) ‹‹ራስን የመለወጥ ምሥጢር››

1 comment:

  1. ቀጥይበት እኔም ይህን የመሰለ ሳይት ብሎገር እንዲያጎለብትልኝ እርጅግ

    ReplyDelete