Saturday 20 October 2012

በትግሌ ያገኘኋት ኳስ ናት ብሎ ለብቻው ተጫውቶ ለብቻው ነው የሚያገባው

አገሪቱን የሚመራው ማን እንደሆነ ሳይታወቅ ዝም ብሎ ይፃፋል እንዴ? የኢህአዴግ ሊ/መንበርና የአገሪቱ Prime minister እስኪታወቅ ድረስ ፈርቼ ግን እንዳይመስላችሁ፡፡ እንዴት እፈራለሁ…ኢህአዴግ እያለልኝ (ይቅርታ ህገ መንግስቱ እያለልኝ ማለቴ ነው!)

በነገራችን ላይ አዲሱ ጠ/ሚኒስትር እንዴት ናቸው? በቀደም ፓርላማ ውስጥ የምክር ቤቱ አባላት ለሰነዘሯቸው ጥያቄዎች መልስና ማብራሪያ ሲሰጡ ይመቹ ነበር አይደል! መቼም አንደበተ ርዕቱ ናቸው! (ከወንበሩ ይሆን እንዴ?) ደሞም እኮ የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር “ግርፍ” ናቸው ይባላል (ይባላል ነው!) ከመምህሩ ደቀመዝሙሩ እንዳይሆን እንጂ የተማረውን ልቅም አድርጎ የሚይዝ ተማሪ ሸጋ አይደለም እንዴ?! አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ምን ሲሉ ሰማኋቸው መሰላችሁ… “የቀድሞውን ጠ/ሚኒስትር መጥቀስ አበዙ” (ሌኒንን ይጥቀሱ እንዴ ታዲያ!) ለነገሩ ላለፉት ጠ/ሚኒስትር ያለቀስነው ከልባችን ከሆነ እሳቸውን የመሰለ ማግኘት ለምን ይከፋናል?!
 
እኔ የምለው … አቶ ሃይለማርያም ሥልጣን በቃኝ ብለው ወደ ትምህርታቸው ሊገቡ ሲሉ “ከትግሉ ማፈግፈግ የለም” ብለው የመለሷቸው የቀድሞው ጠ/ሚኒስትር ናቸው የሚባለው እውነት ነው እንዴ?

 
በነገራችን ላይ ኢህአዴግ፤ አባላቱ ሥልጣን “በቃን” ሲሉ “ከትግሉ ማፈግፈግ የለም” እያለ ችክ የሚለውን ነገር ቢተው ነው የሚሻለው (ዕድሜ ለመተካካት!) ምን የሚያሳስብ ነገር አለ? አንድ ጥያቄ አለኝ … ግን ለምንድነው ኢህአዴግ ሁሉን ነገር ትግል የሚያደርገው? እኔ ያልገባኝ ምን መሰላችሁ … “አገር መምራት እንዴት ትግል ሊሆን ይችላል?” የሚለው ነገር ነው፡፡ እኔማ ኢህአዴግ አዲስ አበባ ገብቶ ሥልጣን የያዘ ዕለት ትግል አብቅቷል ብዬ ነበር (ተሳስቻለሁ!) እንዴት ብትሉ … ይሄው ፓርቲው 21 ዓመት ሙሉ ከአፉ ላይ ትግል የሚለው ቃል ጠፍቶ አያውቅም፡፡ “ታጋይ ቢሞት ትግል አይሞትም”፣ “ያለመስዋዕትነት ድል የለም”፣ “በእነገሌ መቃብር ላይ ትግሉ ይለመልማል!” ... እነዚህን መፈክሮች መቼም የምንተዋቸው አይመስለኝም!!  ኢህአዴግ እውነት ትግል ላይ ከሆነ ደግሞ ሌሎች ተቃዋሚ ፓርቲዎችን በሰላማዊ መንገድ እንዲንቀሳቀሱ ለምን ያሳስባል? አንድ ጥርጣሬ ግን አለኝ፡፡
 
 ይህች “ትግል” የምትባል ነገር የልማታዊ መንግስት ባህርይ ልትሆን ትችላለች እኮ!

አያችሁ…እኔም ራሴ ዋና ጉዳዬን ትቼ ትግል ውስጥ ገባሁ፡፡ እንግዲህ ወጋችን በአዲሱ ጠ/ሚኒስትራችን ዙሪያም አይደል (መብታችን መሰለኝ!) በመጀመሪያ ግን “ሹመት ያዳብር” ብያለሁ - ለተከበሩ ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ!! እንዴ የስንቱ ወዳጅ አገር መሪ “ሹመት ያዳብር” ሲላቸው እኛ እኮ ዝም አልን! የይገባናል ጥያቄ ወይም ቅሬታ ካለን (የሥልጣን ማለቴ ነው) የ2007 ምርጫ ጊዜ ያደርሰናል፡፡ እኔ የምለው … ተቃዋሚዎች አዲሱን ጠ/ሚኒስትር “Congra!” ብለዋል እንዴ? በአደባባይ ባይሆንም በምስጢር ካሉም በቂ ነው (ነግ በኔ እኮ ነው!) የተከበሩ አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ ገና ጠ/ሚኒስትር ከመሆናቸው በፊት በአዲስ አበባ መስተዳድር ቲቪ ቀርበው ስለአገራችን ተቃዋሚዎች ያሉትን ሰምታችኋል? “አይገቡኝም!” (ልብ በሉ “አይረቡም” አላሉም) ደሞ በደፈናው “አይገቡኝም” ብለው አላለፉም፡፡ “አማራጭ ፖሊሲ ሳይኖራቸው ኢህአዴግን ለመቃወም ብቻ የሚቃወሙ ናቸው” ሲሉ አስረድተዋል - ምክንያታቸውን፡፡ ሁሉንም ግን አላሉም፤ “ከጥቂቶች በቀር” የሚል ጨምረውበታል፡፡ እንደነገርኳችሁ ይሄን የተናገሩት የአገሪቱን ትልቁን ሥልጣን ከመያዛቸው በፊት ነው፡፡ አሁን ግን በደንብ ሊያውቋቸውና ሊገቧቸውም ይገባል - ተቃዋሚ ፓርቲዎች፡፡ (ካልገቧቸው ችግር ነዋ!)
 
እኔ የምለው ግን…የሰሞኑን የፓርላማ ማብራሪያቸውን እንዴት አያችሁት?  ጠ/ሚኒስትሩ ንግግር ላይ ባይታሙም ቀልድና ተረብ ይጐድላቸዋል የሚል ስጋት ያዘለ አስተያየት አንዳንድ ሰንዝረዋል፡፡ እኔም አስተያየታቸውን በከፊል እጋራቸዋለሁ፡፡ ግን ደግሞ ይሄን ያህል ስጋት ውስጥ የሚጥል አይደለም - ጉድለታቸው!! ሥልጣኑን በደንብ ሲለምዱትና ሲለምዳቸው ቀልድና ተረብ ብቻ ሳይሆን ሃይለቃልም ሌላ ሌላም መልመዳቸው አይቀርም (ለመሪነት አስፈላጊ ነው የተባለውን ሁሉ!) ለጊዜው ግን ፓርላማ የቀልድና የፌዝ ቦታ አይደለም ብለን ልናልፈው እንችላለን፡፡
 
አዲሱ ጠ/ሚኒስትር በዲሞክራሲ ግንባታ ሂደት ተቃዋሚዎች የድርሻቸውን ማበርከት እንጂ ጣት መቀሰር ፋይዳ የለውም ያሉት፡፡ ችግሩ ግን ተቃዋሚዎች “ሜዳው የት አለ?” እያሉ ነው፡፡ ሜዳውም ኖሮ ኢህአዴግ ኳሷን አልሰጥም ካለ እኮ ዋጋ የለውም፡፡ (አጫዋቹስ የማነው?) አያችሁ … በትግሌ ያገኘኋት ኳስ ናት ብሎ ለብቻው ተጫውቶ ለብቻው ነው የሚያገባው - ራሱ ላይ፡፡ በሌላ ቋንቋ … ጨዋታም የለም፤ ግብም የለም ማለት ነው፡፡

 አዲሱ ጠ/ሚኒስትር ቤተመንግስት አለመግባታቸውን አንድ ካድሬ ወዳጄ አግኝቶኝ ነገሩን ሲያጫውተኝ ነው፡፡ እሱ እንዳለኝ ከሆነ እንግዲህ … ለኢህአዴግ ሁሉም ታጋይ ነው፤ ሥልጣን ራሱ መስዋዕትነት ነው አሉ - ለፓርቲው የሚከፈል፡፡ እናላችሁ … ለእኔና ለእናንተ ነው እንጂ ለኢህአዴግ አዲሱ ጠ/ሚኒስትር አንድ ታጋይ ማለት ናቸው (ባይታገሉም) ስለዚህ ቤ/መንግስት መግባትና አለመግባት ለኢህአዴግ ቁምነገር አይደለም፡፡ የመብትና የፕሮቶኮል ጥያቄዎች ማንሳት ደግሞ ኪራይ ሰብሳቢነት ነው! (ካድሬው እንዳለኝ)
 
“ጠ/ሚኒስትሩ አገር የሚመሩት ከመካኒሳ እየተመላለሱ ነው የሚባለውስ?” ስል ጠየቅሁት - ካድሬ ወዳጄን፡፡

በረዥሙ ሳቀና “ትቀልዳለህ…እኛ እኮ ጫካ ሆነን ነበር ህዝቡን የምንመራው” አለኝና አረፈው፡፡ እኔ ግን አላረፍኩም፤ ሌላ ጥያቄ አስከተልኩ “ያኛው ትግል እኮ ነው፤ ይሄኛው አገር መምራት…” አልኩት፡፡
 
“ለእኛ ሁለቱም ያው ነው፤ ሁሉም ታጋይ ነው፤ ሁሉም መስዋዕትነት ይከፍላል!” አለና ፈገግ አሰኘኝ፡፡

“ግን እኮ መስዋዕትነቱንም ቢሆን ቤተመንግስት ሆነው ቢከፍሉት ይሻላል” ስል መለስኩለት፡፡ ካድሬው ወዳጄ ግን አልተዋጠለትም፡፡ “አልፈርድብህም፤ የኢህአዴግን ባህርይ ስለማታውቅ ነው” ብሎ እኔኑ ጥፋተኛ ሊያደርገኝ ፈለገ፡፡ ወዳጄን ምን ነካው! ራሱ የኢህአዴግን ባህርይ አያውቅም እንዴ? (ድብቅነቱን ማለቴ ነው) የሆኖ ሆኖ ግን እንደምንም ቤ/መንግስት ቢገቡ ይሻላል - ጠ/ሚኒስትሩ፡፡ ሌላው ቢቀር ለወጉ እንኳ! (ወግ ነው ሲዳሩ ማልቀስ እንዳትሉ) መቼም ከ2005 እስከ - ድረስ ጠ/ሚኒስትር ነበሩ መባሉ አይቀርም አይደል (ደሞዟ ባትረባም!) እኔ የምለው…የጠ/ሚኒስትር ደሞዝ ተሻሻለ ወይስ ያው ነው?  ለካስ ኢህአዴግ ሥልጣንን መስዋዕትነት ነው የሚለው ወዶ አይደለም!!

No comments:

Post a Comment