Wednesday 10 October 2012

በከፍተኛ ወጪ የተሠራው መንገድ ለባቡር ግንባታ መፍረሱ አነጋጋሪ ሆኗል

በከፍተኛ ወጪ ተገንብቶ በቅርቡ ለትራፊክ ክፍት የተደረገው የቃሊቲ መስቀል አደባባይ የአስፓልት መንገድ መካከኛው ክፍሉ ለባቡር ሐዲድ ግንባታ ሲባል እየፈረሰ ነው፡፡ የአስፓልቱ መፍረስ በአካባቢው ነዋሪዎች ዘንድ መነጋገሪያ ሆኗል፡፡
በ40 ሜትር ስፋት ከቃሊቲ አደባባይ እስከ መስቀል አደባባይ የተገነባው መንገድ ዘጠኝ ኪሎ ሜትር ርዝመት አለው፡፡ ይህንን መንገድ በ295 ሚሊዮን ብር የገነባው የቻይናው ሲአርቢሲ አዲስ ኢንጂነሪንግ ኩባንያ ነው፡፡ መንገዱ በአንድ ኪሎ ሜትር 32.8 ሚሊዮን ብር ውጭ የተደረገበት ነው፡፡

መንገዱ ሲገነባ መካከለኛው ክፍል ለባቡር መስመር የሚውል መሆኑ እየታወቀ፣ ከፍተኛ ወጪ በማውጣት በአስፓልት መገንባት ለምን አስፈለገ የሚሉ ጥያቄዎች እየተነሱ ነው፡፡ የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ፈቃዱ ኃይሌ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ አስፓልቱ ሳይፈርስ የባቡር መስመሩ በላዩ ላይ ሊገነባ ይችላል፡፡

በዚህ ጉዳይ ላይ ከባቡር መስመሩ ባለቤት የኢትዮጵያ የምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ጋር እየተነጋገሩ መሆኑን ኢንጂነር ፈቃዱ ተናግረዋል፡፡ የባቡር ሐዲዱን የሚገነባው የቻይናው ሬልዋይ ግሩፕ ነው፡፡ ኩባንያው ንፋስ ስልክ ትምህርት ቤት አካባቢ የመንገዱን መካከለኛ ክፍል በማጠር አስፓልቱን እያፈራረሰ ለሐዲድ ግንባታው እያስተካከለ ይገኛል፡፡ የአዲስ አበባ ቀላል የባቡር መስመር ፕሮጀክት አካል በሆኑት ቦታዎች ላይም ግንባታው ተጀምሯል፡፡


ኢንጂነር ፈቃዱ አስፓልቱን አፍርሶ የባቡር መስመሩን መዘርጋት አልተዋጠላቸውም፡፡ ‹‹በሌሎች አገሮች ከባቡር ሐዲድ ሥር አስፓልት አለ፤›› የሚሉት ኢንጂነር ፈቃዱ፣ አስፓልቱ ሳይፈርስ ሐዲዱ ሊዘረጋ እንደሚችል ያላቸውን እምነት ገልጸዋል፡፡ እሳቸው የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ከመሆናቸውም በተጨማሪ፣ የኢትዮጵያ የምድር ባቡር ኮርፖሬሽን የሥራ አመራር ቦርድ አባል ናቸው፡፡

የኢትዮጵያ የምድር ባቡር ኮርፖሬሽን የመሠረተ ልማት ዘርፍ የቀላል ባቡር ፕሮጀክት ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር በኃይሉ ስንታየሁ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ አስፓልቱ የተሠራበት ማቴሪያል የባቡር መስመሩን ለመዘርጋት አያስችልም፡፡ በዚህም ምክንያት የባቡር መስመሩን ለመዘርጋት የግድ አስፓልቱ መፍረስ እንዳለበት አስረድተዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት ከአንድ ሜትር በላይ ተቆፍሮ ሐዲዱን መሸከም በሚያስችለው ደረጃ እየተሠራ መሆኑን ኢንጂነር በኃይሉ ገልጸዋል፡፡ በአዲስ አበባ በተለያዩ ቦታዎች የቀላል ባቡር ዝርጋታ መጀመሩንም አስረድተዋል፡፡

የተጀመረውም በአያት ጦር ኃይሎች ፕሮጀክት አልታድና ዳርማር አካባቢ፣ በሽሮሜዳ ቃሊቲ ፕሮጀክት ደግሞ ንፋስ ስልክ ትምህርት ቤትና ጊዮርጊስ አካባቢዎች ነው፡፡ አጠቃላይ የባቡር መስመር ዝርጋታ ፕሮጀክቱ 475 ሚሊዮን ዶላር እንደሚፈጅ ታውቋል፡፡ ከዚህ ገንዘብ ውስጥ የቻይናው ኩባንያ 75 ሚሊዮን ዶላር በቅድሚያ ተከፍሎታል፡፡

No comments:

Post a Comment